ቀጥታ፡

የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለውጭ ምንዛሬ ግኝትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ሚናውን እየተወጣ ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዘአ)፡- የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደግና ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከተ መሆኑን የተለያዩ አምራቾች ገለጹ፡፡  

የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች በአዲስ አበባና በሸገር ከተሞች የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ጎብኝተዋል።

በዚሁ ወቅት የጎበዝ የፀሐይ ኃይል ሶላር ሴል ማምረቻ ሥራ አስኪያጅ በረከት ኃይሉ፤ ምርታቸውን በዋናነት ለአሜሪካ ገበያ እንዲሁም ወደ ካናዳ፣ ቬትናም እና መካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት እየላኩ መሆኑን ተናግረዋል።


 

ድርጅቱ ለ300 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸው፤ በመንግሥት እየተደረገ ያለው ድጋፍ የማምረት ዐቅማቸውን እንዳሳደገው ለኢዜአ ገልጸዋል።

የዳቺ ማኑፋክቸሪንግ ቺፍ ኮሜርሻል ኦፊሰር ቢንያም ዮሐንስ በበኩላቸው ድርጅቱ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ወደ ምርት መግባቱን አውስተው፤ በአራት ፋብሪካዎች 46 ዓይነት የታሸጉ ምግቦችን እያመረተ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።


 

ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከመደገፍ ባለፈ፣ በውጭ ምንዛሬ ግኝት ረገድ የበኩሉን አስተዋጽዖ እያበረከተ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት።

መንግሥት እያደረገ ያለው ድጋፍና ክትትልም የድርጅቱን የማምረት ዐቅም እንዳሳደገው አረጋግጠዋል።

ድርጅታቸው የተለያዩ የስፖርት ትጥቆችንና አልባሳትን እያመረተ እንደሚገኝ የገለጹት ደግሞ የሀብቴ ጋርመንት ምክትል ሥራ አስፈፃሚ ሐይማኖት ሙሉጌታ ናቸው።


 

ከሀገር ውስጥ አቅርቦት ባለፈ፤ ምርቶቻቸውን ጋና፣ ላይቤሪያ እና ቡሩንዲን ጨምሮ ወደ ተለያዩ ሀገራት እየላኩ መሆናቸውን አስረድተዋል።

በአሁኑ ወቅት ድርጅቱ 400 ሠራተኞች ያሉት ሲሆን፤ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሠራተኞችን ቁጥር በ50 በመቶ ለማሳደግ እየሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል።

የካይት ማኑፋክቸሪንግ የግዢና ሽያጭ ኃላፊ አሸናፊ ፀጋ በበኩላቸው፤ ድርጅቱ የተለያዩ የምርት ማሸጊያዎችን በማምረት ለተለያዩ ኢንዱስትሪዎች እያቀረበ ነው ብለዋል።


 

እስካሁን ለ220 ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም ጠቁመዋል።

መንግሥት የመሬትና የፋይናንስ አቅርቦትን ጨምሮ እያደረገ ያለው ድጋፍ ድርጅቱ የማምረት ዐቅሙን እንዲያሳድግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያደረገ መሆኑንም አመላክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም