የፌዴራል መንግሥት ተንዳሆን ከችግር አውጥቶ ወደ ልማት አውታር መልሶታል - ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ - ኢዜአ አማርኛ
የፌዴራል መንግሥት ተንዳሆን ከችግር አውጥቶ ወደ ልማት አውታር መልሶታል - ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የፌዴራል መንግሥት ተንዳሆን ከችግርና ስጋት አውጥቶ የአፋርን ክልል ተጠቃሚ ወደሚያደርግ የልማት አውታር መልሶታል ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ ገለጹ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በአፋር ክልል የተንዳሆ መስኖ መሠረተ ልማት ማጠናቀቂያና መልሶ ግንባታ ፕሮጀክትን መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል።
የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የተንዳሆ የመስኖ ፕሮጀክት ዱብቲ፣ የሠመራ ሎጊያ ክፍለ ከተሞችን ጨምሮ ስድስት ወረዳዎችን በቀጥታ ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል።
የአፋር ሕዝብ በአዋሽ ወንዝ ጎርፍና በድርቅ በውሃ እጥረት ጉዳት ሲደርስበት መቆየቱን አንስተው፤ አሁን ግን ችግሩ እየተቀረፈ ነው ብለዋል።
የተንዳሆ ግድብ ውሃ ሲሞላ የማስተንፈሻ ቦዩ የመቆጣጠሪያ ሥርዓቱ የተስተካከለ ስላልነበር ማህበረሰቡ ላይ ትልቅ የጎርፍ ስጋት ሆኖ እንደነበር አስታውሰዋል።
በመሆኑም የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አፋርን ከጎርፍ አደጋ እየታደገና የውሃ አቅምን በመጠቀም የውሃ እጥረትን እየፈታ መሆኑን ተናግረዋል።
ለፌደራል መንግሥቱ ትልቅ አድናቆት አለኝ ያሉት ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ፤ በቢሊየን ሀብት አውጥቶ ተንዳሆን ወደዚህ ደረጃ ማድረሱ ቀላል አይደለም ነው ያሉት።
በአፋር ክልል በርካታ የቆላማ ልማትና የመስኖ ግድቦች እየተገነቡ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም የፌዴራል መንግሥቱን አመሥግነዋል።