በክልሉ የገቢ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገት የማፋጠን ስራ ይጠናከራል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ የገቢ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገት የማፋጠን ስራ ይጠናከራል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
ሀዋሳ ፤መጋቢት 19/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የገቢ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገት የማፋጠን ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ገለጹ።
በክልሉ የሞዴል ግብር ከፋዮች የእውቅናና የሽልማት መርሃ ግብር በሀዋሳ ከተማ ተካሂዷል።
ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ክልሉ ሲመሰረት የነበረው የ4 ቢሊዮን ብር የገቢ አቅም በአሁኑ ወቅት ከ40 በመቶ በላይ እድገት አሳይቷል።
የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመንና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ለህዝቡ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በዚህ ሂደትም የታማኝ ግብር ከፋዮች ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰው፤ "ግብር ከፋዮች የሀገር ባለውለታ በመሆናቸው ክብር ይገባቸዋል" ብለዋል።
በሀዋሳ ከተማ የታየው ፈጣን የመሰረተ ልማት ለውጥ የታማኝ ግብር ከፋዮች ውጤት መሆኑን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በሌሎች የክልሉ አካባቢዎች ያለውን የኢኮኖሚ አቅም በአግባቡ ለመጠቀም አመራሩ ተግቶ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል።
የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ደምሴ እሳቱ በበኩላቸው፤ በ2017 የግብር ዘመን 14 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ገልጸው፤ ይህም ከቀደመው ዓመት የ4 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል።
በተያዘው የ2018 በጀት ዓመት ስምንት ወራት ውስጥም 14 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የእቅዱን 94 በመቶ ማሳካት ተችሏል ብለዋል።
ለዚህ ስኬት በቴክኖሎጂ የተደገፈ የገቢ አሰባሰብ ስርዓት መዘርጋቱና የሞዴል ግብር ከፋዮች ታማኝነት ትልቅ ሚና ማበርከቱን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
በ2017 የግብር ዘመን ከ57 ሚሊዮን ብር በላይ በመክፈል ግንባር ቀደም የሆኑት የኢታብ ሳሙና ፋብሪካ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር መምህር ተስፋዬ አበበ፤ ግብርን በታማኝነት መክፈል ሀገራዊ ግዴታና የድርጅቱ ባህል መሆኑን ተናግረዋል።
የዘላለም ኮንስትራክሽን ባለቤት ኢንጂነር ዘላለም ወልደአማኑኤል በበኩላቸው፤ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈላቸው እውቅና እንደተሰጣቸው ገልጸው፤ መንግስት የሚሰበስበው ገቢ በከተሞች የመሰረተ ልማትና በኮሪደር ልማት ስራዎች ላይ እያመጣ ያለውን ለውጥ በምሳሌነት ጠቅሰዋል።
በዕለቱ እውቅናና ሽልማት የተሰጣቸው 77 የደረጃ "ሀ" እና "ለ" ግብር ከፋዮች፣ የልማት ድርጅቶችና የህብረት ስራ ማህበራት ሲሆኑ፤ እነዚህ አካላት ከ700 ሺህ እስከ 57 ሚሊዮን ብር ግብር የከፈሉ መሆናቸው ታውቋል።