በሸገር ከተማ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግበር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ትኩረት ተሰጥቷል - ኢዜአ አማርኛ
በሸገር ከተማ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግበር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ትኩረት ተሰጥቷል
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግበር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የሸገር ከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) ገለጹ።
በከተማው የአርሶ አደሮች መሠረታዊ የኑሮ ማሻሻያ ሁኔታ ላይ ያተኮረ ወርክሾፕ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።
ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ ባለፉት ሦስት ዓመታት ጥናትን መሠረት በማድረግ የሸገር ከተማን ለማሳደግና ለማዘመን የተለያዩ ተግባራት ሲከናወኑ ቆይተዋል።
በቴክኖሎጂ የታገዙ ተግባራትን በማከናወን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማስመዝገብ ትኩረት እንደተሰጠው ጠቁመው፤ ከተማው ከተመሰረተ ጀምሮ ዘመናዊ ፕላንን ጨምሮ ከተማዋን የማዘመን ስራዎች ስኬታማ እየሆኑ መምጣታቸውን አብራርተዋል።
በተለይም የከተማውን አርሶ አደር የአኗኗር ዘይቤ በማሻሸል በኩል ወርክሾፑ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህም በእቅድና በአፈፃፀም መካከል ያለውን ክፍተት ለማጥበብ፣ ልማቱን በተጨባጭ መረጃ ለመመዘንና የተገኘውን ለውጥ ለማስቀጠል ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።
በአጠቃላይ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግባር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
የሸገር ከተማ አስተዳደር ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመድ ቶፊቅ በበኩላቸው፤ ከተማው አርሶ አደሩን ማዕከል ባደረገ አዲስ እሳቤ የተመሰረተ መሆኑን ተናግረዋል።
የአርሶ አደሩን ሕይወት ለመለወጥና ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ጥናቶች እየተከናወኑ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ከተማውንና አርሶ አደሩን በማቀራረብ የነበረውን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ስብራት ለመጠገን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ አርሶ አደሮችን ከእርሻ ስራ ወደ ኢንዱስትሪ፣ የእንስሳት እርባታ፣ ንግድና አገልግሎት ዘርፎች ለማሸጋገር በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
በወርክሾፑ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምግብ ዋስትና ዘርፍ ተመራማሪ መስከረም አቢ፤ ከተሜነት የኢኮኖሚ እድገትን በማፋጠን በኩል ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል።
የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻል እንደ ትምህርትና ጤና ያሉ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ምርትና ምርታማነትን መጨመር እና የቁጠባ ባህልን ማሳደግ ላይ በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነትና የከተማዋን እድገት አመዛዝኖ ማስኬድ ለከተማዋ ዘላቂ ስኬት ወሳኝ መሆኑን ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል።