ቀጥታ፡

ሳይንስና ቴክኖሎጂ የኢኮኖሚው ምሶሶ እንዲሆን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምር የመደገፍ ተግባራቸውን ማጠናከር አለባቸው

ሮቤ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ ሳይንስና ቴክኖሎጂ በሀገር ኢኮኖሚ ውስጥ መሪ ሚና እንዲጫወት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምር የመደገፍ ተግባራቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ።

የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በቴክኖሎጂ ፈጠራና ኢንተርፕረነርሺፕ ላይ አዳዲስ የፈጠራ ሀሳቦችና ግኝቶች ላሏቸው ወጣቶች ሲሰጥ የቆየውን ተግባር ተኮር ሥልጠና በማጠናቀቅ የእውቅና መርሐ ግብር አካሄዷል።


 

በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትርና የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ሳይንስና ቴክኖሎጂ በሀገር ኢኮኖሚ ውስጥ መሪ ሚና እንዲጫወት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምር የመደገፍ ተግባራቸውን ማጠናከር ይገባቸዋል።

ሚኒስቴሩ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የኢኮኖሚው ምሶሶ እንዲሆን በሀገር ደረጃ የተቀረጸውን ፖሊሲ ተግባራዊ ለማድረግ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አክለዋል።

በተለይ ክህሎትና አዳዲስ የፈጠራ ሀሳብና ግኝት ያላቸውን ወጣቶች በማወዳደር ፕሮጀክቶቻቸው በሀገር ኢኮኖሚ ውስጥ ተጨባጭ ለውጥ እንዲያመጣ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።

ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ በ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂ፣ በኢኖቬሽንና የፈጠራ ምህዳርን በማስፋትና በዘርፉ የዳበረ ማህበረሰብ በመፍጠር ረገድ በተከናወኑ ሥራዎች አበረታች ለውጦች መታየታቸውን አመልክተዋል።

በተለይ ጀማሪ ሥራ ፈጣሪዎች በሥራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ የሚያበረታታ "ስታርት አፕ አክት" የተሰኘ የሕግ ማዕቀፍ እንዲኖረውና የፋይናንስ ድጋፍ በማግኘት ወደ ኢኮኖሚ እንዲቀየር እየተደረገ መሆኑን በማሳያነት አንስተዋል።

በአሁኑ ወቅትም በሀገር አቀፍ ደረጃ ባለፉት ዓመታት በዘርፉ የተገኙ ውጤቶችን ይበልጥ በማጠናከር ከወቅቱ ዓለም ዓቀፋዊ ሁኔታ ጋር የተናበበና በዘርፉ እመርታዊ ለውጥ ለማምጣት ያለመ የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ሚኒስቴሩ ከመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር አዳዲስ የፈጠራ ሀሳቦችና ግኝቶች ላሏቸው ወጣቶች ያዘጋጀው የእውቅና መድረክ የዚሁ ጥረት አካልና ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል።


 

የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ብቁ ዜጎችን ለማፍራት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በተለይም ዩኒቨርሲቲው በባሌ፣ በምስራቅ ባሌና በምዕራብ አርሲ ዞኖች በሚገኙ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የቴክኖሎጂ ዝንባሌ ያላቸውን ተማሪዎች በመመልመል የክህሎት ሥልጠና እንዲያገኙ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል።

በዚህም በዩኒቨርሲቲው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ማዕከል ሥልጠና ያገኙ ተማሪዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ በ2017 ዓ.ም በተካሄደው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውድድር አንደኛ ደረጃን በመያዝ ሽልማትና እውቅና ማግኘታቸው የዘርፉ ትኩረት ውጤት መሆኑን ለአብነት አንስተዋል።

በአሁኑ ወቅትም አዳዲስ የፈጠራ ሀሳብና ግኝት ያላቸው ግለሰቦች በሥራቸው ስኬታማ እንዲሆኑና ሊያጋጥሟቸው የሚችሉ ተግዳሮቶችን እንዲረዱ የተሰጠው የአቅም ግንባታ ሥልጠና የጥረቱ አካል መሆኑን ፕሬዚዳንቱ አክለዋል።

እውቅና ያገኙ የፈጠራ ባለቤት የሆኑ ወጣቶች በበኩላቸው ያገኙት ተጨማሪ ዕውቀትና እውቅና የበለጠ ለመስራት የሚያነሳሳቸው መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም