ቀጥታ፡

በጽኑ መሠረት ላይ እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ከተሜነት እና ክትመት ለትውልድ የተሻለ ኑሮ መሠረት ነው - የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በጽኑ መሠረት ላይ እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ከተሜነት እና ክትመት ለትውልድ የተሻለ ኑሮ እና ለሀገር ብልጽግና መሠረት መሆኑን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስገነዘበ።

አገልግሎቱ በማኅበራዊ ትሥሠር ገጹ ባጋራው መረጃ፤ ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለው መጠነ ሰፊ የከተሞችና የኮሪደር ልማት ሥራ የሀገሪቱን ገጽታ ከመለወጥ ባለፈ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የተወሰደ ታሪካዊ እርምጃ ነው ብሏል። 

የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ያጋራው መረጃ ሙሉ ቃል ቀጥሎ ቀርቧል፡-

በፅኑ መሠረት ላይ እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ከተሜነት እና ክትመት ለትውልድ የተሻለ ኑሮ እና ለሀገር ብልጽግና መሰረት ነው፡፡

መጋቢት 18/2018 ዓ.ም የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
ኢትዮጵያ እያከናወነችው ያለው መጠነ ሰፊ የከተሞችና የኮሪደር ልማት ሥራ የአገሪቱን ገጽታ ከመለወጥ ባለፈ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የተወሰደ ታሪካዊ እርምጃ ነው። 

ከተሞች ለረዥም ዘመናት ተቆራኝቷቸው የነበረውን የጉስቁልና መልክ ከመቀየር አኳያ እና  ለነዋሪዎቻቸው ምቹ እና ማራኪ ሆነው እንዲደራጁ ማድረግ በሚያስችል ሁኔታ መንግስት ከፍተኛ በጀት በመመደብ እና የሰው ሀይል በማደራጀት ትኩረት ሰጥቶ መስራት ተችሏል፡፡ 

በተለይም በአዲስ አበባ እና በሌሎች ትላልቅ ከተሞች እና ገጠራማ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉት የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች፣ የከተማ ማደስ፣ አካባቢዎችን የማስዋብ ስራዎች፣ በመልሶ ማልማት የታሪካዊ ቦታዎች እና የቅርስ ጥገናዎች ማካሄድ እንዲሁም የኮሪደር ልማት ሥራዎች በጉልህ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ 

በመሰረተ ልማት ዝርጋታ ስራዎች ማህበረሰቡ በንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት፣ የተሻሻለ መንገድ፣ ደረጃውን የጠበቀ የጤና አጠባበቅ ስርዓት፣ ጥራት ያለው ትምህርት እና የሀይል አቅርቦት እንዲያገኝ በማድረግ ረገድ የተሰሩት ቅንጅታዊ ስራዎች ውጤታማ እና መንግስት ከህብረተሰቡ ይነሱ የነበሩትን የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ጥያቄዎችን ምላሽ ለመስጠት ያደረገውን ከፍተኛ ጥረት በተጨባጭ ያሳዩ ናቸው፡፡ 

በሌላም በኩል በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አቅጣጫ ሰጪነት ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት በርካታ የልማት ስራዎች የተከናወኑ ሲሆን ከተማን የማስዋብ ስራ በስፋት ከተሰራባቸው መካከል አንዱ እና ዋነኛ ተጠቃሽ ሆኖ ይገኛል፡፡ 

በተለይ ለኮሪደር ልማት እና ከተማ ማደስ ስራዎች የተሰጠው ትኩረት በኢትዮጵያ ታላላቅ ከተሞች ብቻ ሳይሆን በ78 ከተሞች ነው የተተገበረው። 

የኮሪደር ልማቱ በሀገሪቷ የሚገኙትን ከተሞች ኃላ ቀር የኑሮ ስርዓት በመቀየር ዘመናዊነትን የተላበሰ የአኗኗር ስልት እንዲፈጠር ከማስቻሉም ባሻገር በአየር ንብረት ጥበቃ፣ በአመለካከት ለውጥ፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ ምቹ የኑሮ አካባቢን ከመፍጠር፣ በቱሪስት መስህብነት እና ጤናማ ማህበረሰብ እንዲኖር ከማስቻል አኳያ የራሱን ትሩፋት ያበረከተ ነው፡፡ በዚህም የዜጎችን ጥሩ የመኖር ተስፋን ያለመለመ ከመሆን አልፎ የኩራት ምንጭ ለመሆን የበቃ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሌሎች ሀገራት ዜጎችም አድናቆት እና ምስክርነት በእጅጉ የጎላ ለመሆን በቅቷል፡፡ 

የቅርስ ጥገናዎች ላይ ታሪካዊ እሴቶቻቸውን በመጠበቅ የተደረገው መልሶ ማልማት ወይም እድሳት በተጠና ሁኔታ ለትውልድ ማስተላለፍ በሚያስችል እና የከተሞችን ውበት በማጉላት የቱሪዝም መስህብነታቸውን እንዲጨምሩ ያስቻለ ለመሆን አስችሏል፡፡ በዚህም በርካታ ቱሪስቶች በኢትዮጵያ የሚያደርጉትን የቆይታ ጊዜያቸውን በማራዘም ከፍተኛ የገቢ ምንጭ ማግኛ መንገድ የሚሆንበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡

እነዚህን የብልጽግና ትሩፋቶች አጠናክሮ ከማስቀጠል አኳያ የበለጠ ትኩረት ሰጥቶ መስራት የሚጠይቅ ነው የሚሆነው፡፡ የኢትዮጵያን አፍሪካዊ የብልጽግና ተምሳሌትነት እና ርዕዩዋን ለማሳካትም የዜጎች ተሳትፎ ወሳኝ በመሆኑ ከእስካሁኑ የትብብር መንፈስ በላቀ ሁኔታ አስተዋጽኦ በማበርከት የኢትዮጵያን ቀጣይ የስኬት መንገድ ዕውን ለማድረግ መረባረብ የሚገባ ይሆናል፡፡ 

በአጠቃላይ ኢትዮጵያ የጀመረችው የከተማነት ብልጽግና ጉዞ መጪውን ትውልድ ታሳቢ በማድረግ ጭምር የተከናወነ ሲሆን መንግሥት የዲጂታል ቴክኖሎጂንና ዘመናዊ አሰራርን በማጣመር፣ ከተሞቻችን የቱሪስት እና የኢንቨስትመንት መዳረሻ ከመሆን አልፈው ለነዋሪዎች የሥራ ዕድል ፈጠራ ማዕከል፣ ምቹ እና የኩራት ምንጭ እንዲሆኑ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ያረጋግጣል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም