ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል

አዲስ አበባ፤መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከማስገኘቱም በላይ ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ሰፊ ዕድል እየፈጠረ እንደሚገኝ የኢትዮጵያና ቻይና የወዳጅነትና የትብብር ኮሚቴ ሰብሳቢ ረዳት ዣንግ ሊንግሊንግ ገለጹ።

"ኢትዮጵያ ለቢዝነስ ዝግጁ ናት" በሚል መሪ ሀሳብ ኢንቨስት በኢትዮጵያ' ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።

በዚሁ ፎረም ላይ ለመሳተፍ የመጡት የኢትዮጵያና ቻይና የወዳጅነትና የትብብር ኮሚቴ አባላት የኢትዮጵያን ብሄራዊ ሙዚየም ጎብኝተዋል።

የኢትዮጵያና ቻይና የወዳጅነትና የትብብር ኮሚቴ ሰብሳቢ ረዳት ዣንግ ሊንግሊንግ በዚሁ ወቅት፤የሰው ዘር መገኛ የሆነችውን የኢትዮጵያን ብሔራዊ ሙዚየም በመመልከታቸው ከፍተኛ ደስታ ተሰምቷቸዋል።

በአዲስ አበባ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ዘመናዊና የአፍሪካ የውበት ማዕከል ማድረጉን ያደነቁት ሰብሳቢዋ፣ በከተማዋ የታየው ለውጥ እጅግ አስደናቂ መሆኑን ጠቁመዋል።

የሁለቱ ሀገራት ወዳጅነት ጠንካራ መሆኑን ገልጸው፤ በርካታ ቻይናውያን በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን እያፈሰሱ እንደሚገኙና ኮሚቴውም ለዚህ ስኬት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አብራርተዋል::

በቀጣይም ኮሚቴው ስለ ኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት አማራጮችን የማስተዋወቅ ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።

ኢትዮጵያ የጀመረችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሀገሪቷ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከማስገኘቱም በላይ ለቀጥታ የውጭ ኢንቨስትመንት ሰፊ ዕድል መፍጠሩም ተናግረዋል። 

መንግስት የቻይና ባለሀብቶችን ወደ ሀገር ውስጥ ለመሳብ የፈጠረው ምቹ ሁኔታና እያደረገ ያለው ጥሪ የሚደነቅ ነው ብለዋል።

ሌላኛው የፊልም ዳይሬክተሩ ሱን ካይካይ በበኩሉ፤ በኢትዮጵያ በሚቆይበት ጊዜ በካሜራው የቀረጻቸውን ምስሎች በማሰባሰብ ወደ ሀገሩ ሲመለስ ዘጋቢ ፊልም ለማዘጋጀት ማቀዱን ገለጿል።
 
ዳይሬክተሩ በአዲስ አበባ ከተማ ባደረገው እንቅስቃሴ የተመለከተው የከተማዋ ውበትና ፅዳት እጅግ አስደንቆታል።

በቻይና ሄንግዲያን ከተማ የኢትዮጵያን ቡና በማስተዋወቅ ላይ የምትገኘው አርቲስት ሃኦ ሊፒንግ፣ የሁለቱ ሀገራት የወዳጅነትና የትብብር ኮሚቴ በቤጂንግ በሚያዘጋጃቸው የኢንቨስትመንት ፎረሞች አማካኝነት ስለ ኢትዮጵያ የተሻለ እውቀት ማግኘቷን ገልጻች።

አርቲስቷ ኢትዮጵያ የሰው ዘር ብቻ ሳይሆን የቡናም መገኛ መሆኗን ካወቀች በኋላ ቡናውን እጅግ በመውደዷ በማስተዋወቅ ስራው ላይ በንቃት እየተሳተፈች እንደምትገኝም ጠቁማለች። 

ዛሬ በኢትዮጵያ ምድር በአካል ተገኝታ በመጎብኘቷም የተሰማትን ታላቅ ደስታ ገልጻለች።

በቱሪዝም ሚኒስቴር የማይስ ቱሪዝም ሽያጭ ዴስክ ኃላፊ ብዙዓለም ጌቱ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚዬም የአብዛኛው የሰው ዘር ቅሪተ አካል መገኛ በመሆኑ በዓለም ደረጃ ልዩ እንደሚያደርገው ገልጸዋል።

ጎብኚዎችና ኢንቨስተሮች እንዲህ ያሉ የኢትዮጵያን ቀዳሚነት የሚያሳዩ ስፍራዎችን መመልከታቸው ስለ ሀገሪቷ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ትልቅ በር እንደሚከፍትም አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም