በባሕር ዳር እና ጎንደር እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከተሞቹን ወደ ላቀ ዕድገት የሚያሸጋግሩ ናቸው - ኢዜአ አማርኛ
በባሕር ዳር እና ጎንደር እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከተሞቹን ወደ ላቀ ዕድገት የሚያሸጋግሩ ናቸው
አዲስ አበባ፤መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፡-በባሕር ዳር እና በጎንደር ከተሞች እየተከናወኑ የሚገኙ መጠነ ሰፊ የልማት ስራዎች፣ከተሞቹን ወደ ላቀ የእድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ መሆናቸውን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን በሁለቱ ከተሞች የተከናወኑ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በሥፍራው ተገኝተው በሰጡት ማብራሪያ፤ጉብኝቱ ቀደም ብለው የተጀመሩ ግዙፍ ስራዎች ያለሙትን ግብ ማሳካታቸውን ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
በባሕር ዳር ከተማ ጣናን ለዕይታ ግልጽ የሚያደርገው የኮሪደር ልማት የመጀመሪያ ምዕራፍ በስኬት መጠናቀቁን ጠቁመው፤ይህም ልማት ከውበት ባለፈ የከተማዋን የአየር ሁኔታ የቀየረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከመሠረተ ልማት ዝርጋታ አኳያ የብስክሌት፣የአስፋልት እና የእግረኛ መንገዶች ግንባታ መጠናቀቁን ጠቅሰው፤ በመንገዶቹ ግራና ቀኝ የገበያ ማዕከላትን የመገንባት ስራ በተጠናከረ ሁኔታ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
በስፖርት ዘርፉም የሶስት ትልልቅ እግር ኳስ ሜዳዎች ግንባታ በዚህ ዓመት ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃ ጠቅሰው፥እየተገነቡ ያሉ የቱሪስት መዳረሻዎችና የመዝናኛ ስፍራዎች የከተማዋን እድገት ይበልጥ እንደሚያፋጥኑም አረጋግጠዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በጎንደር ከተማ ባደረጉት ጉብኝት፣ ከአጼ ፋሲል ቤተ መንግስት ጀምሮ ትልልቅ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።
በተለይም በርካታ ቱሪስቶችና ምዕመናን የሚታደሙበት የጥምቀት ባህር አካባቢን የማልማት ስራ በፍጥነት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ የገበያ ስፍራዎችና የስፖርት ማዘውተሪያዎች ግንባታ ጎን ለጎን የተለያዩ ታሪካዊ ቅርሶችን የማደስ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።
እነዚህ ስራዎች አጠቃላይ የጎንደርን የቱሪስት ማዕከልነት ይበልጥ የሚያጠናክሩ ናቸው ብለዋል፡፡
ሌላኛው የጉብኝቱ አካል የነበረው የመገጭ ግድብ ግንባታውን በቀሩት የዓመቱ ወራት ለማጠናቀቅ የሚያስችል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ግድቡ ጥራት ባለው ሁኔታ እየተገነባ መሆኑን መመልከታቸውን ገልጸው፤ በሂደቱ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የሚያስችል የተደራጀ የስራ ክፍፍል መደረጉን አመላክተዋል።
ግድቡ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ለአካባቢው ማህበረሰብ ዘርፈ ብዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎችን እንደሚያስገኝም አክለው ገልጸዋል።