ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የባሕር በር ባይተዋርነት ምላሽ የሚያገኝበት ጊዜ እሩቅ አይደለም 

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሕጋዊ፣ ታሪካዊና መልክዓ-ምድራዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄና ባይተዋርነት ምላሽ የሚያገኝበት ጊዜ እሩቅ አይደለም ሲሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገለጹ፡፡  

የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በማስከበር የህዝብን አንድነት ለማስቀጠል በሚደረገው ጥረት የሚጠበቅባቸውን ገንቢ ሚና እንደሚወጡም አረጋግጠዋል። 

ብሔራዊ ጥቅም የሀገርን ሉዓላዊ የግዛት አንድነት፣ የኢኮኖሚ ዕድገትና የማኅበራዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ የዜጎች ሀገራዊ ግብ ነው፡፡

የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄና ሀገራዊ ምክክር ሂደቶች ስኬታማነትም የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም በማስከበር ጠንካራ ሀገረ መንግስትን የሚያጸኑ የጋራ አጀንዳዎች ናቸው።

የፖለቲካ ፓርቲዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ የተለያየ የፖለቲካ ርዕዮተ-ዓለም ቢኖራቸውም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በማስከበር ረገድ ልዩነት ሊኖር አይገባም፡፡


 

የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መለሰ ዓለሙ የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ከብሔራዊ ጥቅም ጋር የተሰናሰለ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊና መልክዓ-ምድራዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ መርህን የተከተለና የማይቀለበስ የህዝብ አጀንዳ መሆኑን ገልጸው፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባይተዋርነት ምላሽ የሚያገኝበት ጊዜ እሩቅ አይደለም ብለዋል፡፡

የወሎ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ፕሬዝዳንት ነጻነት ጣሰው፤ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ማስከበርና የህዝብን አንድነት ማስቀጠል የፖለቲካ መታገያ ማዕከላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡


 

የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ምላሽ ማስገኘት የሀገር ክብርና ህልውና ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፤ ብሔራዊ ጥቅምን ማስከበር ለድርድር የማይቀርብ የጋራ አቋማቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነት ፓርቲ ፕሬዝደንት ዘሪሁን ገብረእግዚአብሔር በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና የህዝብ አንድነት ለድርድር የማይቀርቡ ቀይ መስመሮች ናቸው ብለዋል፡፡


 

የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ማስመለስን ጨምሮ የሀገርን ብሔራዊ ጥቅምና የህዝብን አንድነት ለማስቀጠል በሚደረገው ጥረት ሁሉ የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም