የኮደርስ ስልጠና መውሰዳችን ተጨማሪ እውቀትና ክህሎት ከማግኘት ባለፈ በዘርፉ ብቁ ተወዳዳሪ መሆን አስችሎናል - ኢዜአ አማርኛ
የኮደርስ ስልጠና መውሰዳችን ተጨማሪ እውቀትና ክህሎት ከማግኘት ባለፈ በዘርፉ ብቁ ተወዳዳሪ መሆን አስችሎናል
መቀሌ፤ መጋቢት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና መውሰዳችን ተጨማሪ እውቀትና ክህሎት ከማግኘት ባለፈ በዘርፉ ብቁ ተወዳዳሪ እንድንሆን አስችሎናል ሲሉ በመቀሌ ከተማ የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ ወጣቶች ተናገሩ።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተመቻቸው የአምስት ሚሊየን የኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠና በተለይም ወጣቶች የእድሉ ተጠቃሚ ሆነው ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነታቸውን የሚያሳድግ መሆኑ ይታወቃል።
የስልጠናው ዓላማ በዘርፉ የዜጎችን አቅም ከመገንባት ባለፈ ኢትዮጵያ በዘርፉ ልማት የጀመረችው እድገትና ማንሰራራት ቀጣይነት እንዲኖረው የሚያደርግም ነው።
በዚህም መሰረት በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ዜጎች ስልጠናውን እየወሰዱ ከራሳቸው አልፈው ለሀገራቸው የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ትግበራ አሻራቸውን እያኖሩ መሆኑ ይታወቃል።
በዚሁ መሰረት በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ ስልጠናውን የወሰዱ ወጣቶች የኮደርስ ስልጠና በመውሰዳችን ተጨማሪ እውቀትና ክህሎት ከማግኘት ባለፈ በዘርፉ ብቁ ተወዳዳሪ መሆን አስችሎናል ብለዋል።
አስተያየታቸውን ከሰጡ ወጣቶች መካከል ወጣት አኸዛ ወልደጊወርጊስ፤ የኮደርስ ስልጠና በመውሰድ በዘርፉ የተሻለ ክህሎትና እውቀት ያገኘችበት መልካም እድል መሆኑን ገልፃለች።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁ ተወዳዳሪ በመሆን ከራስ ተጠቃሚነት አልፎ በዲጂታል የአገልገሎት ዘርፍ ጥራትና ፍጥነት ያለው አገልግሎት ለመስጠትም ወሳኝ መሆኑን ተናግራለች።
ስልጠናውን ከወሰዱ ወጣቶች መካከል ሰሎሞን ገብረመድህን እና ጸጋአብ ገብረእግዛብሄር፤ የኮደርስ ስልጠናው በተለይም ለወጣቶች መልካም እድል ይዞ የመጣ መሆኑን ተናግረዋል።
ስልጠናውን በመውሰዳቸው በዘርፉ ብቁ ተወዳዳሪ እና የስራ እድል ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን በተግባር አይተነዋል ያሉት ወጣቶቹ ሌሎችም ጊዜ ሳያባክኑ እድሉን እንዲጠቀሙበት መክረዋል።
የኮደርስ ስልጠናው የዳታ ሳይንስ፣ ዌብ ፕሮግራሚንግ፣ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስና አንድሮይድ የማበልጸግ እና ሌሎች ተያያዥ ዕውቀቶችን ማግኘት የሚያስችል መሆኑ ይታወቃል።