በክልሉ ከ458 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ተከናውኗል-ቢሮው - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ ከ458 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ተከናውኗል-ቢሮው
ባህርዳር ፤መጋቢት 15 /2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በዘንድሮው የበጋ ወራት በአርሶ አደሩ ተሳትፎ በ458 ሺህ 794 ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መከናወኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ ።
የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ በዘንድሮ የበጋ ወራት ከዘጠኝ ሺህ የሚበልጡ ተፋሰሶችን መሰረት ያደረገ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ተካሂዷል።
በዚህም ከ458 ሺህ 794 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የማሳና የጋራ ላይ ዕርከን ስራዎችን መከናወናቸውን ጠቅሰዋል።
እንዲሁም ከ91 ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱና የተጎዱ ተራራማ ቦታዎችን በመከለል ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተጠብቀው መልሰው እንዲያገግሙ መደረጉንም አመልክተዋል ።
በተጨማሪም ከ7 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ የተለያዩ የውሃ ማስረጊያ ስትራክቸሮች መከናወናቸውን ጠቁመው የውሃ ማፋሰሻና መቀልበሻ ቦዮች ግንባታ ስራዎችም መካሄዳቸውን ተናግረዋል ።
አርሶ አደሩ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በየጊዜው እየተረዳ በመምጣቱ ከዕቅድ በላይ ስራውን መፈፀም እንደተቻለም አስታውቀዋል።
በመጭው የክረምት ወቅት በበጋ ወራት የተከናወነውን የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በስነ-ህይወታዊ ዘዴ ለማጠናከር ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አመላክተዋል።
በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ዓለሙ ይግዛው እንዳሉት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መስራት ከተጀመረ ወዲህ የተራቆቱ መሬቶች ደን መልበስ ጀምረዋል ። የእርሻ መሬቶችም የአፈር ለምነታቸው እንዲጨምርና የሰብል ምርታማነት እየተሻሻለ እንዲመጣ ማስቻሉንም ገልፀዋል።
የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ በየዓመቱ እየሰራን እንገኛለን ያሉት ደግሞ በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የጓንጓ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙሉነህ ይግዛው ናቸው።
ባለፉት ዓመታት በሰራነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተፋሰሶች በማገገማቸው ለእንስሳት ዋነኛ የመኖ ምንጭ ሆነዋል ብለዋል።