ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው ለዘላቂ ልማትና ብልፅግና ወሳኝ መሰረት ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው ለዘላቂ ልማትና ብልፅግና ወሳኝ መሰረት መሆኑን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ ገለፁ።

የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ከአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ''የሃይድሮ ዲፕሎማሲና ቀጣናዊ ትብብር ለዘላቂ ውኃና ኢነርጂ ልማትና አስተዳደር'' በሚል መሪ ሃሳብ መጋቢት 14 እና 15 ቀን 2018 ዓ.ም ቀጣናዊ ጉባኤ በቢሾፍቱ ከተማ እየተካሄደ ነው።


 

በዚህ ወቅት የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊ፣ ሕጋዊ መሰረት ያለው መሆኑን አንስተዋል።

ከ120 ሚሊየን በላይ ህዝብ ያላት ሀገር የባህር በር ማጣቷ ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ እንዳለው ጠቁመው፤ የባህር በር ጉዳይ የመልማት ጥያቄ መሆኑን አስረድተዋል።

የባህር በር ለሀገር ብልጽግና ወሳኝ መሰረት መሆኑን አንስተው፤ በፍጥነት እድገት እያስመዘገበች ላለችው ኢትዮጵያ እጅግ አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ አሁን ላይ የባህር በር ባለቤትነቷን ለማስመለስ የምታደርገው ጥረት ቀደም ብሎ የተሰራውን ታሪካዊ ስህተት የማረም ተግባር ነው ብለዋል።

ትውልዱ ለዘላቂ ልማትና ብልጽግና መረጋገጥ የባህር በር ሚና የማይተካ መሆኑን መገንዘብ እንዳለበት ጠቅሰው፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዓለም አቀፍ ህግ የሚደገፍ እንደሆነም ተናግረዋል።

በጉባዔው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢዎችና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ(ዶ/ር)፣ የአፍሪካ ሀገራት የውሃ ሚኒስትሮች፣ የዘርፉ ተመራማሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም