በባህር ዳር የአውሮፕላን ማረፊያ ማስፋፊያን ጨምሮ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በባህር ዳር የአውሮፕላን ማረፊያ ማስፋፊያን ጨምሮ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው
አዲስ አበባ፤መጋቢት 13/2018(ኢዜአ)፦ በባህር ዳር የአውሮፕላን ማረፊያ ማስፋፊያን ጨምሮ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው ሲሉ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በባህርዳር እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት፣ የመንገድ መሰረተ ልማት እና የአየር መንገድ ፕሮጀክቶችን ተመልክተዋል።
በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት የባህር ዳር ከተማን የቱሪዝም እና የኢኮኖሚ ማዕከልነት ይበልጥ የሚያጎሉ ግዙፍ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በጥሩ አፈፃፀም ላይ ይገኛሉ ብለዋል።
ከአሮጌው የዓባይ ድልድይ እስከ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የሚደርሰውና 2 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው አዲሱ የኮሪደር ልማት ስራ በዚህ ሳምንት ተጀምሮ በአበረታች ጉዞ ላይ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በከተማዋ ከገብርኤል እስከ ምድረ ገነት 1 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 30 ሜትር ስፋት ያለው የአስፓልት መንገድ ግንባታም ተጠናቋል።
ከሃኒ ጋርደን እስከ ወረብ ድረስ 4 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለውና የአዲሱ የዓባይ ድልድይ መዳረሻ አስፓልት ስራም ተጠናቆ ለአገልግሎት ዝግጁ መሆኑን ተመልክተናል ነው ያሉት።
በሌላ በኩል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በባህርዳር እያከናወናቸው ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችንም ጎብኝተዋል።
በየካቲት 2016 ዓ.ም ከ1 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ወጪ ተመድቦለት የተጀመረው የባህርዳር የአብራሪዎች ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ከአየር መንገዱ ግዙፍ ፕሮጀክቶች አንዱ ሲሆን በአሁኑ ወቅት 91 በመቶ አፈፃፀም ላይ ይገኛል።
ማሰልጠኛው ዘመናዊ የመማሪያ ክፍሎች፣ የአሠልጣኞችና የተማሪዎች መኖሪያ ህንፃዎች፣ የስፖርት ማዘውተሪያዎችን ያካተተ ሲሆን፣ በሚቀጥለው ወር ሙሉ ለሙሉ ይጠናቀቃል ተብሏል።
በባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ማስፋፊያ ፕሮጀክት እየተገነባ የሚገኘው አዲሱ ተርሚናል ግንባታው 81 ነጥብ 58 በመቶ ደርሷል።
ይህ አዲሱ ተርሚናል በሰዓት እስከ 1 ሺህ መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እነዚህ ፕሮጀክቶች ሲጠናቀቁ የከተማዋን ገፅታ ከመቀየር ባለፈ ለኢኮኖሚ ዕድገት የጎላ ፋይዳ እንዳላቸው ገልጸዋል።
በተለይም የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአብራሪዎች ማሰልጠኛ እና የኤርፖርት ማስፋፊያ ስራዎች ለአካባቢው ብቻ ሳይሆን ለሀገራዊ ብልፅግናችን ትልቅ አቅም ይሆናሉ ነው ያሉት።
ባህር ዳርን የአፍሪካ የቱሪዝም እና የትራንስፖርት መዳረሻ የማድረግ ጉዞን አንድ እርምጃ ወደፊት እንደሚያሻግሩትም አንስተዋል።