ቀጥታ፡

በኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተተገበሩ የግብርና ምርታማነት ኢንሼቲቮች አስደማሚ ውጤት እያስገኙ ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ምርታማነት ኢንሼቲቮች አስደማሚ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን በኢትዮጵያ የአየርላንድ ኤምባሲ ምክትል የሚሲዮን መሪ ፈርጋል ራያን ገለጹ፡፡

በኢትዮጵያና አየርላንድ መካከል የተገነባውን ታሪካዊ ወዳጅነት በግብርና የትብብር መስክ የበለጠ ለማጠናከር በቁርጠኝነት እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል።

ፈርጋል ራያን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያና አየርላንድ በጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ትብብር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት ናቸው ብለዋል።

ይህ ዘመናትን የተሻገረ ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት በግብርና ምርታማነት ትብብር ተጠናክሮ መቀጠሉንም ገልጸዋል።

አየርላንድ በድንች ሃብት ልማት ያካበተችውን ልምድና ተሞክሮ ለኢትዮጵያ በማጋራት የዘርፉ ምርታማነት የሚሻሻልበትን ድጋፍ እያደረገች መሆኗን አንስተዋል።

በዚህም የሀገራቱ የሁለትዮሽ ትብብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን የሚቋቋም የምርምር ውጤቶችን በማውጣት የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት እንዲሻሻል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃና ባለአነስተኛ የመሬት ይዞታ አርሶ አደሮችን የሰብል ምርታማነት አቅም በማጎልበት የምግብ ዋስትናን እያረጋገጠ እንደሚገኝ አብራርተዋል።

በቀጣይም ሀገራቸው በግብርና ዘርፍ ያላትን ምርጥ ተሞክሮ በማጋራት የኢትጵያን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለማፋጠን በቁርጠኝነት እንደምትሰራ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያንና አየርላንድን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ትብብር በማጠናከር የግብርና ሙያተኞችን ለማብቃት እንደሚሰራም አንስተዋል።

ከበርካታ ዓመታት በፊት አየርላንድ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ በግብርና ምርታማነት ላይ የተፈጠረባት ጫና በዜጎች የምግብ ደኅንነት ላይ ተፅዕኖ አሳድሮ እንደነበር አስታውሰዋል።

በዚህም መነሻነት በግብርና ዘርፍ የተደረጉ ዘርፈ ብዙ የኢንቨስትመንት ተነሳሽነቶች ያመጡት ለውጥ የበለጸገችና እራሷን የቻለች አየርላንድን መፍጠር እንዳስቻለ አብራርተዋል።

በኢትዮጵያም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ምርታማነት ኢንሼቲቮች አስደማሚ ስኬቶችን እያስገኙ እንደሚገኝ አንስተዋል።

የመንግስትና ዜጎች የግብርና ምርታማነትን የማሳደግ ቁርጠኝነትም የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥ የሚያስችል ምቹ መደላድል መፍጠር እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም