ቀጥታ፡

ድሬዳዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል--ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ

ድሬዳዋ፤መጋቢት 10/ 2018 (ኢዜአ)፡-ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ድሬዳዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ ተናገሩ።

የአስተዳደሩ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች በድሬዳዋ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት ተጠናክረው በሚቀጥሉበት ሁኔታዎች ላይ ዛሬ መክረዋል። 


 

አመራሮቹ በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በድሬዳዋ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተመልክተው በሰጡት የሥራ አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ምክክር አድርገዋል።

መድረኩን የመሩት የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ እንዳሉት፤ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ ድሬዳዋን ለኑሮ፣ ለሥራ፣ ለኢንቨስትመንትና ለንግድ ተመራጭ ለማድረግ በተከናወኑ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። 

የድሬዳዋን ታሪካዊ ሃብቶችና ቅርሶች በጠበቀ መንገድ በጥራት የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ለከተማዋ ድምቀት ከመሆን ባለፈ ለኢንቨስትመንት እና ለቱሪዝም ዘርፍ መጎልበት ወሳኝ ሚና እያበረከቱ ነው ብለዋል።

በተጨማሪም በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተሰሩ ሥራዎች በርካታ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት በመሸጋገር በሺህ ለሚቆጠሩ ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ተኪ ምርቶችን በማምረት ለድሬዳዋ እድገት ወሳኝ ሚና እየተጫወቱ መሆኑን አስረድተዋል።

እነዚህን ውጤታማ ሥራዎች በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በተቀናጀ መንገድ ለመሰብሰብ መረባረብ ይገባል ሲሉም ከንቲባው አስገንዝበዋል።


 

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ በበኩላቸው እንዳሉት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በድሬዳዋ ያደረጉት የሥራ ጉብኝትና የሰጡት የሥራ አቅጣጫ በየደረጃው በሚገኘው አመራርና ነዋሪ ላይ ከፍተኛ  የሥራ መነሳሳት ፈጥሯል።

በተለይ በአስተዳደሩ የተጀመሩ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት በማጠናቀቅ ድሬዳዋን የብልጽግና ግቦች የተሳካባት ቀዳሚ ከተማ ለማድረግ የተቀናጀ እንቅስቃሴ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።

በኮሪደር ልማት፣ በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና በገጠሩ ክፍል የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ፕሮጀክቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውም ጠቅሰዋል። 

በቀጣይ በየደረጃው ያለው አመራር በህዝብ ተሳትፎ የተራቆቱ ተራራማ አካባቢዎችን አረንጓዴ የማልበስና ድሬዳዋን ከተፈጥሮ አደጋ የመታደግ ጅምር ሥራዎችን ለማሳደግ በቁርጠኝነት ሊተጋ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። 

በተጨማሪም ወጣቶችን የሥራ ባለቤት የማድረግ እንዲሁም ጅምር የፍራፍሬና የአትክልት ልማቶችን የማላቅ ጉዳይ ትኩረት ይሰጣቸዋል ብለዋል። 

በየዘርፉ ውጤታማነትን ለማስቀጠል የተለጠጠ የገቢ አሰባሰብ ዕቅድ ተዘጋጅቶ በተቀናጀ መንገድ መተግበር ቀዳሚ ጉዳይ መሆኑንም አቶ ኢብራሂም አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም