የኮሪደር እና መልሶ ማልማት አነስተኛ ቢዝነሶችን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ለስራ እና ለሸማቹ ሳቢ በሆነ መንገድ መልሶ በመገንባት የተሰራ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኮሪደር እና መልሶ ማልማት አነስተኛ ቢዝነሶችን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ለስራ እና ለሸማቹ ሳቢ በሆነ መንገድ መልሶ በመገንባት የተሰራ ነው
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማትና መልሶ ማልማት ስራ አነስተኛ ቢዝነሶችን የሚያዳክም ሳይሆን፣ ይበልጥ ዘመናዊ፣ ለስራ እና ለሸማቹ ሳቢ በሆነ መንገድ መልሶ በመገንባት የተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት በአጠቃላይ እስከ አሁን በተሰራው 5 ሺህ 490 ያህል አዳዲስ ንግድ ሱቆችን የተገነቡ እና ነባሮቹንም ከመንገድ setback ወደ ኋላ በመሳብ እንደገና በአዲስ መልክ እንዲገነቡ መደረጉን ጠቅሰዋል።
ከእነዚህም ውስጥ 2 ሺህ 800 ያህሉ እንደ አዲስ የተገነቡ፣ ቀሪዎቹ 2 ሺህ 690 ደግሞ ከመንገድ setback ወደ ኋላ በመሳብ እንደገና በአዲስ መልክ ደረጃቸውን በማሻሻል የተገነቡ ናቸው ብለዋል።
ከዚህ ውስጥ 55 በመቶ የሚሆነው ግንባታ በባለቤቶቹ መገንባታቸውን ገልጸው፤ ቀሪውን በቀበሌ እና በቤቶች ኮርፖሬሽን ውስጥ ሲነግዱ ለነበሩ መንግስት ገንብቶ ለልማት ተነሺዎች ያስረከባቸው መሆናቸውን አስታውቀዋል።
እንዲሁም መሬት ለመውሰድ ፍቃደኛ የሆኑት ደግሞ በአክሲዮን ተደራጅተው እንዲገነቡ እያደረግን ነው ብለዋል።
በመሆኑም ከተማዋ ለንግድ ስራ ቀላል፣ ይበልጥ ሳቢና ምቹ መደረጓን ጠቅሰው፤ የቢዝነስ እንቅስቃሴው እንዲዳከም አለመደረጉንም ገልጸዋል።
ከንቲባዋ በመልዕክታቸው ልክ በሌሎቹ ኮሪደሮች እንዳደረግነው ሁሉ ትላንት ማምሻውን በይፋ ክፍት የተደረገው የድል ፕላዛ እና የቁርጡሚ ወንዝ ዳርቻ የልማት ተነሺዎችን አስተናግደንበታል ብለዋል።
ቀደም ሲል ከቦሌ አትላስ እስከ ብራስ መንገድ በኮሪደር ልማቱ ምክንያት ተነስተው የነበሩ የንግድ ተቋማት፣ አሁን በዚሁ ፕላዛ ውስጥ ስራቸውን በስኬት ጀምረዋል ሲሉም ገልጸዋል።