ቀጥታ፡

በኦሮሚያ ክልል የተሻሻሉና የአካባቢን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረጉ የቡና ችግኞች ይተከላሉ

ሮቤ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የተሻሻሉና የአካባቢን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረጉ የቡና ችግኞች እንደሚተከሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትልና የቡናና ፍራፍሬ ዘርፍ አስተባባሪ መሐመድሳኒ አሚን ገለጹ።

አቶ መሐመድሳኒ አሚን በክልሉ ባለፉት ዓመታት የቡና ምርት እና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች ሲናወኑ መቆየታቸውንና በተያዘው የበልግ የዝናብ ወቅት የተዘጋጁ የቡና ችግኞችን ከ300ሺህ በሄክታር በሚበልጥ አዲስ መሬት ላይ ይለማሉ ብለዋል።

የቡና ዝርያዎቹ ከግብርና ምርምር ተቋማት የተለቀቁ እንዲሁም የአካባቢን ስነ-ምህዳር ከግምት ያስገቡ እና የተሻለ ምርት የሚሰጡ መሆናቸውንም ለኢዜአ ገልጸዋል።

ስራውን ስኬታማ ለማድረግ በየደረጃው ከሚገኙ የግብርና ሀላፊዎች እና ባለሙያዎች ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል።

በክልሉ ባሌ ዞን የቡና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ የተሻሻሉ የቡና ዝርያ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ሙአዊያ ፉአድ ናቸው።

ከግብርና ምርምር ማዕከላት የወጡ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በስፋት መትከል የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።

እነዚህን ዝርያዎች በመጠቀም ባለፉት ሰባት ወራት በወረዳዎቹ በተደረገው እንቅስቃሴ ከ41 ሚሊየን በላይ የተሻሻሉ የቡና ዝርያ ያላቸው ችግኞች ማዘጋጀት መቻሉን አስረድተዋል።

በአሁኑ ወቅት በዞኑ እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም የቡና ችግኝ ተከላ መጀመሩን ገልጸው በዚህም 5ሺህ 700 ሔክታር አዲስ መሬት እንደሚለማ አስታውቀዋል።

በልማቱም ከ20 ሺህ በላይ አርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን ጠቁመው የቡና ችግኝ ተከላውም ከአዲስ መሬት በተጨማሪ ያረጁና ከምርት ውጭ የሆኑ የቡና ተክሎችን በመንቀል ጭምር በምትኩ ተከላው እንደሚካሄድ አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም