ቀጥታ፡

የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶች የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና አይቀሬነት የሚያረጋግጡ ናቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶች የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና አይቀሬነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ድል ፕላዛ እና የቁርጡሜ የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶችን መርቀው ከፍተዋል።

በምረቃው ባስተላለፉት መልዕክት፤ የስሉጥ ከተሜነት መገለጫ ለነዋሪዎች ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ምቹ የአገልግሎት ምኅዳር መፍጠር መሆኑን አስገንዝበዋል።

በዋናነትም የከተሜነት የአኗኗር ሥርዓት ፅዳትና ውበት የተላበሰ የአረንጓዴ ስፍራ፣ ለዜጎችና ተሽከርካሪዎች ምቹ የእንቅስቃሴና ጤናማ የመኖሪያ ምኅዳር መፍጠር ማለት እንደሆነም ገልጸዋል።


 

በአዲስ አበባ ቴዎድሮስ አደባባይ ለምረቃ የበቁ ፕሮጀክቶችም የአረንጓዴ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳ፣ የህጻናት መጫወቻና መናፈሻዎችን አሟልቶ የተገነባ መሆኑን አስተውቀዋል።

በዚህም የድል ፕላዛ እና የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶች ግንባታም የከተሜነት መስፈርትን በማሟላት ለመዲናዋ ተጨማሪ ድምቀት ለመሆን እንደበቁ ተናግረዋል።

የተገነቡ መሰረተ ልማቶች አካባቢውን ውብ ገጽታ በማላበስ የመሬት ውስጥ ባለሦስት ወለል ሕንጻ 500 ተሽከርካሪዎችን በአንድ ጊዜ ማስተናገድ የሚችል አቅም እንዳለው አስረድተዋል።

አካባቢው ውብና ማራኪ ገጽታ መላበሱም ለመዲናዋ የንግድና ቱሪዝም ልማት እንቅስቃሴ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግና አይቀሬ ነው ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ ለዚህም በልማት መስክ የተፈጠረው የትብብር አቅም ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት እየጣለ ነው ብለዋል።


 

የአዲስ አበባ አስደናቂ የልማት ስኬቶች የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና አይቀሬነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የዮድ አቢሲንያ ባህል ማዕከል ባለቤት ትዕዛዙ ኮሬ በበኩላቸው፤ አዲስ አበባ ታሪክና ማንነቷን በሚገልጥ አስደናቂ የለውጥ ጉዞ ላይ ናት ብለዋል።

መንግስት ለግሉ ዘርፍ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የፈጠረው አስቻይ ሁኔታም የአልሚ ባለሃብቶችን ተነሳሽነትና አቅም በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እየመጣ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም