ቀጥታ፡

‎በሲዳማ ክልል በሞዴል መንደሮች ግንባታ የገጠሩን ማህበረሰብ ኑሮ ለማሻሻል የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል

‎ሀዋሳ፤ የካቲት 29/2018(ኢዜአ)፦ ‎በሲዳማ ክልል ሞዴል መንደሮችን በማስፋፋት የገጠሩን ማህበረሰብ ሕይወት ለማዘመን የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ።

የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመተባበር ያስገነባው ዘመናዊ የገጠር መንደር በሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ እና በፕላንና ልማት ሚኒስትሯ ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ተመርቋል።

በክልሉ ዳራ ወረዳ መጪሾ ቀበሌ የተገነባ ሞዴል መንደር አቅመ ደካማ ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው።

በምረቃ መርሀግብሩ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ እንዳሉት በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች ሞዴል መንደሮችን በማስፋፋት ህብረተሰቡ የተሻለ ኑሮ እንዲኖረው ለማድረግ እየተሰራ ነው።

‎በመንደሩ የተገነቡት ቤቶች ዘመናዊ ከመሆናቸው ባለፈ የስልጡን ማህበረሰብ መስፈርቶችን ያሟሉ በመሆናቸው ብልጽግናን በሁሉም አካባቢዎች ለማድረስ የሚደረጉ ጥረቶች ማሳያ ናቸው ብለዋል።

የመደመር መንግሥት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን አንስተው የመጪሾ ሞዴል የገጠር መንደርም የዚሁ ጥረት ውጤት መሆኑን ገልፀዋል።

‎በክልሉ ዛሬ ከተመረቀው በተጨማሪ የግንባታ ስራ የተጀመረባቸው ወረዳዎች እንዳሉና ተስፋፍቶ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።

‎የአርሶ አደሩን የኢኮኖሚ አቅም ከማሳደግ ባለፈ ዘመናዊ ሕይወት እንዲኖረው ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን የገለጹት አቶ ደስታ፣ የሌማት ትሩፋትን ጨምሮ የግብርናን ምርታማነት ለማሳደግ በተሰራው ስራ ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል።

‎የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው ሞዴል መንደሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የገጠር ኮሪደር ልማት እሳቤ በመነሳትና ቀደም ተብሎ ከተሰሩ ልማቶች ልምድ በመውሰድ የተገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል።

‎ቤቶቹ የውሃ፣ የፀሐይና የባዮ ጋዝ ኃይል ያላቸው መሆኑን ጠቅሰው፤ የወተት፣ የዶሮና ሌሎች የሌማት ቱሩፋት ሥራዎችን ለማከናወን የሚያስችሉ ግንባታዎችን ያካተቱ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

ሞዴል መንደሮቹ የገጠሩን ማህበረሰብ አኗኗር ወደዘመናዊነት ለመቀየር የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልፀው፤ በሁሉም አካባቢ መስፋት እንዳለባቸው አመልክተዋል።

የመደመር መንግስት የገጠር አካባቢ ነዋሪዎችም ዘመናዊ አኗኗርን እንዲከተሉ በትኩረት እየሰራ ስለመሆኑ አንስተው በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።

‎በሞዴል መንደሩ አምስት ዘመናዊ ቤቶች የተገነቡ ሲሆን እያንዳንዳቸው በ1ሺህ 200 ካሬ ሜትር ላይ ያረፉ እንደሆኑም ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም