ቀጥታ፡

የጅግጅጋ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው

ጅግጅጋ፤ የካቲት 28/2018(ኢዜአ)፦ የጅግጅጋ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ከማድረግ ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት መሆኑን ነዋሪዎች ተናገሩ።

በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደር ልማት በክልሎችም እየተስፋፋ ስማርት፣ ምቹና ዘመናዊ ከተሞችን እውን የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል።

ፕሮጀክቱ የከተማችን ብቻ ሳይሆን የሀገራችን ኩራትና ገጽታን የሚቀይር ስኬት ነው -ከንቲባ አዳነች አቤቤ 

ለአኗኗርና ለእንቅስቃሴ አስቸጋሪ የነበሩ ከተሞች በኮሪደር ልማት የብስክሌትና እግረኛ መንገዶችን ጨምሮ የመዝናኛ እና የመጫወቻ ስፍራዎችን በማካተት እየተሰሩ ይገኛሉ።

በዚህ የልማት እቅድ ተጠቃሚ ከሆኑ ከተሞች መካከል በምስራቅ ኢትዮጵያ በንግድ እንቅስቃሴዋ የምትጠቀሰው ጂግጂጋ ከተማ አንዷ ነች። 

የጂግጂጋ ከተማ የኮሪደር ልማት ታሪካዊ ይዘቷ ሳይለቅ፣ ዘመናዊነትን ከባህላዊ እሴቶች ጋር በማሰናሰል የከተማዋን ውበትና መልካም ገጽታ መግለጥ አስችሏል።

በዚህም የከተማዋን የንግድ እንቅስቃሴ ይበልጥ ለማሳለጥና የነዋሪዎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ያስቻለ ዘመን ተሻጋሪ የልማት አሻራ መሆኑን ብዙዎች ይናገራሉ።


 

ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ አህመድ ቡራሌ ፋራህ፤ የኮሪደር ልማቱ በተከናወነባቸው የከተማዋ አካባቢዎች ለንግድም ይሁን ለመዝናኛ ምቹ ሆነው አግኝተናቸዋል ብለዋል።

የእግረኛ፣የብስክሌት እና የተሽከርካሪዎች መንገድ ተለይተው መገንባታቸውን አንስተው በዚህም የትራፊክ አደጋን ለመከላከልና ለሰዎች ነፃ እንቅስቃሴ መልካም እድል ፈጥሯል ሲሉ ተናግረዋል።

ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ሱልጣን አብዲ ከሊፍ፤ የጂግጂጋ ከተማ ለውጥ አስደናቂ እና አስደማሚ መሆኑን ገልጸው መንግስትን አመስግነዋል።


 

ለአካባቢው ከተሞች የልማት ተምሳሌት በመሆን የንግድና የኢንቨስትመንት ልማትን እና የቱሪዝም እንቅስቃሴን ለማሳለጥ የሚያስችል የከተማ ልማት እየተከናወነ ስለመሆኑ አንስተዋል።

ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ተሌህ ደይብ፤ በጂግጂጋ ከተማ የኮሪደር ልማት በተጨማሪ በከተማዋና አካባቢው የሰይድ መሀመድ አብድሌ ሀሰን ሚሞሪያል ፓርክ እና ሌሎችም የመስህብ ስፍራዎች  በአጭር ጊዜ በላቀ ጥራት ተገንብተው መጠናቀቃቸው አስደንቆናል ብለዋል።


 

በሀገር አቀፍ ደረጃ የመጣው ለውጥ በተለይም ለሶማሌ ክልል ልዩ እድል የፈጠረ መሆኑንም አንስተዋል።

በከተማዋ የተሠሩና እየተሠሩ ያሉ መዝናኛ ፓርኮች ከተለያዩ አከባቢዎች የሚመጡ እንግዶች እና የከተማዋ ነዋሪዎች ለመዝናናት ምቹ እድል የሚፈጥሩ መሆኑን ገልጸዋል።

በመሆኑም የተጀመሩ የልማት ሥራዎች  ተጠናክረው መቀጠል ይኖርባቸዋል፤ ለዚህም ድጋፍና ትብብራችን አይለይም ሲሉ አረጋግጠዋል።


 

በከተማዋ የተጠናቀቁ እና በሂደት ላይ ያሉ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች ትልቅ ተስፋ የሰነቅንባቸው ናቸው ያሉት ደግሞ የከተማዋ ነዋሪ መሀመድ ኢብራሂም ናቸው።

በከተማ ልማቱ ለዘመናዊ አኗኗር እና ለጉብኝት ምቹ አካባቢ ከማድረግም ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ይገኛል ብለዋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም