አፍሪካ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈጸመባት በደል የታሪክ ዕውቅና እና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት የምትጠይቅበት ነው - የጋና ፕሬዚዳንት - ኢዜአ አማርኛ
አፍሪካ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈጸመባት በደል የታሪክ ዕውቅና እና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት የምትጠይቅበት ነው - የጋና ፕሬዚዳንት
አዲስ አበባ፤ የካቲት 8/2018 (ኢዜአ)፦አፍሪካ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈጸመባት በደል የታሪክ ዕውቅና እና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት የምትጠይቅበት መሆኑን የጋና ፕሬዚዳንት እና የአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ሻምፒዮን ጆን ድራማኒ ማሃማ ገለጹ።
”ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት የተካሄደው 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል።
ከሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ ጎን ለጎን የጋና ፕሬዚዳንትና የአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ሻምፒዮን ጆን ድራማኒ ማሃማ "የቅድመ አያቶች ዕዳ፣ ዘመናዊ ፍትሕና የአፍሪካውያን ምክንያታዊ የአንድነት ውክልና" በሚል መሪ ሃሳብ መነሻ መግለጫ ሰጥተዋል።
ፕሬዝዳንቱ በመግለጫቸው፤ በአፍሪካ ለተፈጸመው በደል ስርዓታዊ ማካካሻና በዓለም ዓቀፍ ተቋማት ላይ ለምታቀርበው ፍትሀዊ የውክልና ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ሊሰጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በትራንስ-አትላንቲክ የባሪያ ንግድ በአፍሪካውያን ላይ የተፈጸመው ግፍ በሰው ልጅ ታሪክ የታየ ከፍተኛው ኢ-ፍትሀዊ በደል መሆኑን አስታውሰዋል።
ይህ ኢ-ፍትሀዊ በደል ዓለም አቀፍ ዕውቅና ሊሰጠው ይገባል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ ዕውቅና መስጠት መከፋፈል ሳይሆን የሞራል ድፍረትና ፍትሕን የማረጋገጥ የመጀመሪያው እርምጃ ነው ብለዋል።
የአክራ ዳግም ማስጀመር የተሰኘው አሕጉራዊ ንቅናቄ አፍሪካ በውጭ ያላትን የእርዳታ ጥገኝነት ለማስቆም ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም በኮቪድ-19 ወቅት አፍሪካ ክትባት በማግኘት ረገድ የመጨረሻ ተሰላፊ የነበረችበትን አሳዛኝ ሁኔታ በማስታወስ፣ አህጉሪቱ የራሷን የጤና እና የፋይናንስ ተቋማት በራሷ አቅም መገንባት እንዳለባት ገልጸዋል።
የማካካሻ ፍትህን ጥያቄን በተመለከተም ጥያቄው ከገንዘብ ክፍያ ባለፈ የታሪክ መዝገብን የማስተካከልና የተዘረፉ ቅርሶችን የመመለስ ጉዳይ እንደሚጨምር ጠቁመዋል።
አፍሪካ እና የካሪቢያን ሀገራት በዚህ ጉዳይ ላይ በአንድ ድምፅ ለመቆም መስማማታቸውን ገልጸዋል።
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኩል የባሪያ ንግድ በሰው ልጅ ላይ እንደተፈጸመ ወንጀል እውቅና እንዲያገኝ ግፊት እንደሚደረግ አስታውቀዋል።