የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል - ኢዜአ አማርኛ
የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
ወራቤ ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ።
በስልጤ ዞን የተገነባው የሚቶ ኤድነባ መስኖ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማእረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ መሃመድ ኑርዬ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው።
የውሃ አማራጮችን በመጠቀም የመስኖ ልማት በመተግበር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማጎልበት መቻሉን ጠቁመዋል።
ዛሬ ወደ ስራ የገባው የሚቶ ኤድነባ መስኖ ፕሮጀክት የዚሁ አካል መሆኑን አንስተዋል።
ከፍተኛ ወጪ ወጥቶባቸው የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች ደህንነታቸው ተጠብቆ እንዲቆይ ህብረተሰቡ በተገቢው መንገድ መጠቀም እንደሚገባው አስገንዝበዋል።
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ተቋማት ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ካሳዬ ተክሌ፤በተያዘው በጀት አመት በክልሉ 12 የመስኖ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል።
የሚቶ ኤደነባ የመስኖ ፕሮጀክትም በተያዘለት 6 ወራት ጊዜ ውስጥ ግንባታው ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃቱን ገልጸዋል።
ፕሮጀክቱ 54 ሄክታር ማሳ እንደሚያለማና 200 አባወራ እና እማወራዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ጠቁመዋል።
የከርሰ ምድር ውሀን በፀሃይ ሃይል በመሳብ ለመስኖ አገልግሎት እንዲውል የሚያደርገው ፕሮጀክቱ ከ105 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደተደረገበትም ገልጸዋል።
የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ፤ አርሶ አደሮች ይህን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም በዘመናዊ መንገድ አልምተው የቤት ውስጥ ፍጆታን በማሟላት ለውጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች ላይ በማተኮር ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የመስኖ ፕሮጀክቱን ከሚጠቀሙ አርሶ አደሮች መካከል አቶ አብድልሰላም ሃሰን ከሁለት ሄክታር በላይ መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬ ማልማታቸውን ተናግረዋል።
ሌላው አርሶ አደር ሃጅ ዋበላ ተማም በአራት ሄክታር መሬታቸው ላይ ሰብል እና አትክልት ማምረት መጀመራቸውን ገልጸው የመስኖ ፕሮጀክቱን በአግባቡ በመያዝ አገልግሎት እንዲሰጥ በተገቢው መንገድ እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል።
በእለቱም የወራቤ ከተማ አስተዳደር ውስጥ እየተከናወነ ያለው የ1 ነጥብ 6 ኪ.ሜ እንዲሁም ከሚቶ -ባራ- ቡልቡላ ድረስ እየተገነባ ያለው የ38 ኪሎ ሜትር የኮንክሪት አስፋልት መንገድ ግንባታ ያለበት ሁኔታ እንዲሁም የወራቤ ከተማ የወንዝ ዳርቻ ልማት ጉብኝት ተደርጓል።
በስነስርዓቱ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የስልጤ ዞን የስራ ሃላፊዎች እና የአካባቢው ማህበረሰብ ተወካዮች ተሳትፈዋል።