ኢትዮጵያ በግብርና ትራንስፎርሜሽን ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ በግብርና ትራንስፎርሜሽን ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በግብርና ትራንስፎርሜሽንና በምርታማነት ያስመዘገበችው ውጤት ለሌሎች አፍሪካውያን ትልቅ ምሳሌ መሆኑን በአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለጹ።
39ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ "ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት" በሚል መሪ ሀሳብ በመጪው ቅዳሜና እሁድ በአዲስ አበባ ይካሄዳል።
ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ አካታች የአፍሪካ ግብርና ልማት ፕሮግራም (CAADP) እና የዲጂታል ግብርና አስፈላጊነት ላይ መግለጫ ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ የምግብ አመራረት ስርዓቷን ለማጠናከር የጀመረችው አስደናቂ የግብርና ልማት ጉዞ በተለይ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎችም ምሳሌ መሆኑን ገልጸዋል።
ሀገሪቱ ወደ ዘመናዊ ግብርና እየተሸጋገረች ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፥ በዚህም ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ ከየት እንደጀመረች እና አሁን ያለችበትን ደረጃ ተገንዝበናል፤ አሁን ስንዴ ወደ ውጭ በመላክ ላይ ትገኛለች ይህ ትልቅ ስኬት ነው፣ እኛም ይህንን እናደንቃለን ብለዋል።
የኢትዮጵያ ብዝኃ የልማት አጀንዳዎች እንዳሏት በማውሳት፥ ግብርናን ማዘመን ላይም ፈጠራ፣ የፖሊሲ አቅጣጫና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ሲቀናጅ የሚያመጣውን ውጤት ለዓለም አሳይታለች ነው ያሉት።
ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በምግብ ምርቶች ላይ ያላቸውን የውጭ ጥገኝነት ለመቀነስ የኢትዮጵያን ተሞክሮ እንዲከተሉ አስገንዝበዋል።
የአፍሪካን ግብርና ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር በዘርፉ የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ ህብረቱ በዚህ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ የዲጂታል ግብርና ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለአህጉሪቱ አብነት መሆኑን ጠቅሰው ሌሎች አባል ሀገራትም የግብርና ልማትን ማዘመን ቀዳሚ ሥራቸው ሊሆን ይገባል ብለዋል።
እ.አ.አ እስከ 2030 በሚተገበረው የአፍሪካ የዲጂታል ግብርና ስትራቴጂ አማካኝነት በግብርና እሴት ሰንሰለቶች ውስጥ ዲጂታል መሳሪያዎችን ለመተግበር አህጉራዊ ማዕቀፍ እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል።
በቴክኖሎጂ የተደገፉ የዲጂታል የምክር አገልግሎቶች፣ የአየር ንብረት መረጃ ስርዓቶችና የዲጂታል ገበያ ቦታዎች ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና እንዳላቸው ጠቅሰዋል።
ይህም የምግብና ስርዓተ ምግብ ደህንነትን ከማረጋገጥ ባለፈ በተለይ ለወጣቶች ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ነው ያነሱት።
እንደ ኮሚሽነሩ ማብራሪያ የመጀመሪያው የአፍሪካ ህብረት ዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ ከተካሄደ በኋላ፣ የአፍሪካ ህብረት በዘርፉ ዲጂታል ፈጠራን ተቋማዊ ለማድረግ በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየሰራ ይገኛል።