ቀጥታ፡

አፍሪካ በራሷ አቅም የቴክኖሎጂ ስራዎችን በማከናወን ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ የጋራ ጥረትና ርብርብ ማድረግ ይገባል

አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ በራሷ አቅም የቴክኖሎጂ ስራዎችን በማከናወን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ የጋራ ጥረትና ርብርብ ማድረግ እንደሚገባ የአፍሪካ ህብረት የትምህርት፣ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኮሚሽነር ፕሮፌሰር ጋስፓርድ ባንያንኪምቦና ገለፁ።

ኮሚሽነሩ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ሳይንስ ለአፍሪካ አማራጭ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ መሆኑን ገልፀዋል።

ኮሚሽነር ፕሮፌሰር ጋስፓርድ ባንያንኪምቦና በአፍሪካ የትምህርት፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ስትራቴጂ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

በዚህም የትምህርት ተደራሽነት፣ የመምህራን ልማት፣ ጥናትና ምርምሮችን ወደ ንግድ መለወጥ እንዲሁም ከዲጂታልና አረንጓዴ ኢኮኖሚ ጋር የተጣጣመ ክህሎት ማበልጸግ ላይ እንደሚተኮር ገልፀዋል።

አፍሪካ ከተፈጥሮ ሀብት በተጨማሪ ትልቁ ሀብቷ የሰው ኃይል መሆኑን አንስተው፤ ትምህርት ክህሎትን በማሳደግ የአፍሪካን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።

2034 ሁሉም በአፍሪካ ያሉ ህፃናት መሰረታዊ ትምህርት እንዲያገኙ ማድረግ፣ ብቁ መምህራን ማፍራት የሚያስችል ስልጠና መስጠትና ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጥናትና ምርምር እንዲሁም ችግር ፈቺ ስራዎች የሚያበረክቱ መሆን አለባቸው ብለዋል።

የትምህርት ተደራሽነትን እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ስልጠናን ማስፋት ለአረንጓዴና ዲጂታል ኢኮኖሚ አስተዋፅኦ ያለው ዜጋ መፍጠርና የመምህራን ልማት እንዲሁም የመሰረተልማት ውስንነትን ለመፍታት ሰው ሰራሽ አስተውሎትና ቴክኖሎጂ መጠቀም እንደሚገባ ገልፀዋል።  

ዘላቂ የፋይናንስ አቅርቦት ማቅረብ የሚያስችል ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ አህጉር አቀፍ የስትሪንግ ኮሚቴ በማቋቋም እንደሚሰራ ተናግረዋል።  

አፍሪካ ምርምርን ወደ ምርት መቀየር እንዲሁም ፈጠራን ወደ ስራ እድል መፍጠር የሚያስችል ተግባር ማከናወን እንደሚገባ ጠቁመው ለዚህም የሁሉም አጋር አካላት ትብብር ወሳኝ ነው ብለዋል።

አህጉሪቱ በቴክኖሎጂ ራሷን ካልቻለች በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ተወዳዳሪነት ማረጋገጥ እንደማትችልም ነው የገለጹት።

አህጉሪቱ ለሚቀጥሉት አስር ዓመታት የምትመራበትን የሳይንስና ቴክኖሎጂ ስትራቴጂ ይፋ ተደርጓል።

አፍሪካ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ብቻ ሳይሆን ፈጣሪ መሆን አለባት ያሉት ኮሚሽነሩ፣ ህብረቱ የራሱን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስታንዳርድና መመሪያ ማዘጋጀቱን ገልጸዋል።

ይህ መመሪያ ቴክኖሎጂው ከአፍሪካ ባህልና እሴት ጋር ተስማምቶ እንዲለማ የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል።

በአፍሪካ ዩኒቨርሲቲዎች የሚሰሩ ምርምሮች ወደ ምርትና አገልግሎት ተቀይረው ለህብረተሰብ ችግር መፍትሄ እንዲሆኑ ከግል ዘርፉ ጋር ጠንካራ ትስስር እንደሚፈጠር ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም