በበጀት ዓመቱ ያለፉት ስድስት ወራት በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል - ርዕሰ መስተዳድር ኢ/ር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
በበጀት ዓመቱ ያለፉት ስድስት ወራት በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል - ርዕሰ መስተዳድር ኢ/ር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)
ታርጫ፣የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በበጀት ዓመቱ ያለፉት ስድስት ወራት በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ።
የምክር ቤቱ 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤ በታርጫ ከተማ እየተካሄደ ነው።
ርዕሰ መስተዳድሩ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት የስድስት ወራት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት በተሰራው ስራ በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ገልፀዋል።
በበጀት ዓመቱ አጋማሽ በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ጸጋዎችንና የልማት ሀይሎችን በመጠቀም በልማት፣ በሰላምና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ሁለንትናዊ እድገት እንዲመዘገብ ሰፊ ርብርብ ተደርጓል ብለዋል።
በግብርናው ዘርፍ በበ2017/18 ምርት ዘመን ባለፉት ስድስት ወራት 384 ሺህ 160 ሄክታር መሬት በማልማት 20 ሚሊዮን 390 ሺህ 755 ኩንታል ምርት መሰብሰብ መቻሉን ለአብነት አንስተዋል።
በአጠቃላይ የግብርናው ዘርፍ ያለውን አቅም ለመጠቀም በሚደረገው ጥረት አበረታች ውጤቶች እየተመዘገቡ እንዳሉ ጠቅሰው ምርትና ምርታማነትም እያደገ ይገኛል ብለዋል።
በዚህም ከቤት ፍጆታ ባለፈ ገበያን የሚያረጋጋ ምርት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመው ዘርፉን ለማጠናከር የግብርና ግብዓቶችና ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ የማድረግ ስራ በቅንጅት መሰራቱንም አመልክተዋል።
በሌማት ትሩፋት በዶሮ፣ በወተት፣ በዓሳና በማር መንደሮችን ከማደራጀት ባለፈ የእንቁላል፣ የስጋና የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
ባለፉት ስድስት ወራት በመደበኛና ሰው ሰራሽ፣ በተሻሻሉ ኮርማዎች፣ በሲንክሮናይዜሽን ከ30 ሺህ በላይ ላሞችንና ጊደሮችን ማግኘት የተቻለ ሲሆን 2 ሚሊዮን 67 ሺህ 649 የአንድ ቀን ጫጩቶች፣ ቄብና ኮክኔዎችን ማሰራጨት ተችሏል ብለዋል።
በሌላ በኩልም ክልሉን የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ እየተሰራ ሲሆን ባለፉት ስድስት ወራት በአገልግሎት፣ በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፎች ለ57 ባለሀብቶች ፍቃድ መሰጠቱንም በሪፖርታቸው አንስዋል።
ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ በበጀት ዓመቱ ከ18 ቢሊዮን 420 ሚሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ታቅዶ ባለፉት ስድስት ወራት በተደረገው ሰፊ ርብርብ ከ8 ቢሊዮን 358 ሚሊዮን 681 ብር በላይ መሠብሰብ መቻሉን አብራርተዋል።
ገቢው ከተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ84 በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለውም አመልክተዋል።
የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ በበኩላቸው በየደረጃው በሚገኙ ቋሚ ኮሚቴዎች በተደረገ የአስፈፃሚ አካላት ክትትልና ግምገማ የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል።
በተለይም የህዝብ ተጠቃሚነትን የሚያሻሽሉ ተግባራት አፈጻጸም ክትትል ውጤት ማምጣቱን ጠቅሰው ምክር ቤቱ የሚያደርገውን የክትትልና ድጋፍ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
ምክር ቤቱ በሁለት ቀናት ቆይታው፣ የአስፈፃሚ አካላት የስድስት ወራት ሪፖርት በመገምገምና የተለያዩ ሹመቶችንና አዋጆችን በማፅደቅ በሌሎች አጀንዳዎች ላይ እንደሚመክርም ይጠበቃል።