የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በምግብ ራስን ከማስቻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እገዛ እያደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በምግብ ራስን ከማስቻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እገዛ እያደረገ ነው
አርባምንጭ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ) :- በጋሞ ዞን የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በምግብ ራስን ከማስቻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እገዛ እያደረገ መሆኑ ተገለጸ።
በዞኑ ከ1 ሺህ 300 ሄክታር በላይ የበጋ ስንዴ በአርሶ አደሮችና በባለሀብቶች ማሳ እየለማ የሚገኝ ሲሆን የሚጠበቀውን ምርት ለማግኘት የሚያስችል የተባይ ቁጥጥርና እንክብካቤ እየተደረገ እንደሚገኝም ተመልክቷል።
የበጋ ስንዴ ልማት ከተጀመረ ወዲህ ከተረጂነት ወጥተን በምግብ ራሳችንን ለመቻል እየተደረገ ባለው ጥረት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ያሉት ደግሞ በቁጫ ወረዳ ፋንጎ ቀበሌ አርሶ አደር ሚሊዮን በየነ ናቸው።
ከበጋ ስንዴ በሚገኝ ጥቅም ልጆቻችንን ለማስተማርና ኑሮአችን ለመለወጥ ብሎም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ሳንቸገር እንድንከውን አቅም ሆኖናል ብለዋል።
በሁለት ሄክታር መሬት ላይ ስንዴን በመስኖ እያለሙ መሆናቸውን ጠቅሰው የእንክብካቤና የቁጥጥር ስራ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የግብርና ባለሙያዎች ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆኑን ገልጸው በቴክኖሎጂ በመታገዝ ከአንድ ሄክታር ከ40 ኩንታል በላይ ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።
በጋሞ ዞን በምዕራብ አባያ ወረዳ አልጌ ቀበሌ በ20 ሄክታር መሬት ላይ ስንዴ እያለማ የሚገኘው ሳውዝ አግሮ ኢንዱስትሪ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ብሩክ ማማ ምርቱ በጥሩ ቁመና ላይ መሆኑን ገልጸዋል።
ወረዳው የምርጥ ዘር እና የማዳበሪያ እንዲሁም የሙያ ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሰው የስንዴ ምርቱ በምግብ ራስን የመቻል ዕድልን የማስፋት አማራጭ እንደሚሰጥም አስረድተዋል።
ድርጅቱ ከዛሬ 5 ዓመት ጀምሮ ስንዴን በመስኖ በስፋት በማምረት ለአካባቢው መነቃቃት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ጠቅሰው ከዘንድሮው ምርትም ከአንድ ሄክታር 45 ኩንታል ለማግኘት አቅደን እየሠራን እንገኛለን ብለዋል።
የአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ግብርና ባለሙያ አቶ ሳሙኤል ኤርቦ በበኩላቸው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ቴክኖሎጂን በአግባቡ እንዲጠቀም ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስራ የአርሶ አደሩን የግብርና ባህል በመቀየር ጥሪት እንዲያፈሩና ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ እገዛ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል።
የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ሃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት የበጋ መስኖ ስንዴ በምግብ ራስን የመቻል ራዕይን በተጨባጭ እያሳካው ይገኛል ብለዋል።
በተለይ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት አርሶ አደሮች ከተረጂነት ወጥተው የምግብ ሉዓላዊነታቸውን እንዲያረጋግጡ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በዞኑ በተያዘው በጋ ወቅት 1 ሺህ 380 ሄክታር መሬት ስንዴ በመስኖ እየለማ እንደሚገኝ አመልክተው ከዚህም ከ46 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት የሚጠበቅ መሆኑን ገልጸዋል።