ቀጥታ፡

በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ከ102 ሺህ በላይ ቱሪስቶች ሐረሪ ክልልን ጎበኙ

አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡- በ2018 የበጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ከ102 ሺህ 382 በላይ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች ሐረሪ ክልልን መጎብኘታቸውን የክልሉ ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለፁ።

የሐረሪ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት 9ኛ መደበኛ ጉባዔ እየተካሄደ ይገኛል።

በጉባዔው ላይ የክልሉ መንግሥት በ2018 የግማሽ ዓመት ያከናወናቸውን ሥራዎች ሪፖርት ያቀረቡት ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን፤ በቱሪዝም ዘርፍ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል።

የቱሪስት  መዳረሻ  ልማት ሥራዎች፣ የሐረር ዓለም አቀፍ ዕውቅና እንዲሁም እየተከናወኑ ያሉ የማስተዋወቅ ሥራዎች ለከተማው ተጨማሪ ዐቅም ከመፍጠር ባሻገር የቱሪስት ፍሰቱ ብሎም የቆይታ ጊዜ እንዲጨምር ማስቻሉንም አብራርተዋል።

በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ክልሉን ከጎበኙ ቱሪስቶችም ከ226 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ጠቁመዋል።

በአራተኛው ዙር የጀጎል የውስጥ ለውስጥ መንገዶች መልሶ ማልማት ፕሮግራምም፤ በመንግሥታዊ የክልሉ ተቋማት፣ ወረዳዎችና የግል ባለሃብቶች ተሳትፎና ከዘጠኝ ኪሎ ሜትር በላይ የኮሪደር ልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል።

በሌላ በኩል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል።

የመስኖ ልማት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብሮችን በማስፋት፣ የሜካናይዜሽን አጠቃቀምና የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሳደግ የግብርና ዘርፍ ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት መሠራቱንም አንስተዋል።

በዚህም በብርዕና አገዳ ሰብሎች 9 ሺህ 374 ኩንታል በማልማት 150 ሺህ 572 ኩንታል ምርት ማምረት መቻሉን አስታውቀዋል።

የጥራጥሬ ሰብል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሠራው ሥራም 2 ሺህ 295 ኩንታል ቦሎቄ፣ 26 ሺህ 55 ኩንታል የለውዝ እንዲሁም 156 ሺህ 740 ኩንታል የፍራፍሬ ምርት መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት።

እንዲሁም በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በተሠሩ ሥራዎችም 10 የወተት፣ ሁለት የእንቁላል፣ አራት የዓሣ እና ሁለት የማር መንደሮችን መፍጠር መቻሉን በሪፖርቱ አቅርበዋል።

በዚህም 15 ነጥብ 2 ሚሊየን ሊትር ወተት፣ ዘጠኝ ሚሊየን 288 ሺህ እንቁላል፣ 774 ነጥብ 22 ቶን የሥጋ፣ 19 ነጥብ 37 ቶን የማር ምርት ማምረት መቻሉን አክለዋል።

በበጋ መስኖ የአትክልትና የሥራሥር ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በተሠራው ሥራም በሁለት ዙር  2 ሺህ 842 ሔክታር ማልማት ተችሏል ብለዋል።

የሰብል ግብዓት አቅርቦትና አጠቃቀምን ለማሻሻልም 3 ሺህ 931 ኩንታል ሰው ሠራሽ ማዳበሪያ፣ 35 ሺህ 658 ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ኮምፖስት ማቅረብ መቻሉን አመላክተዋል።

በክልሉ የዶሮ ብዜትና ስርጭት ማዕከል 40 ሺህ 500 የዶሮ ጫጩቶችን ማቅረብ መቻሉን ገልጸው፤ የዓሣ ጫጩት ስርጭትን በተመለከተም 28 ሺህ 500 ጫጬቶችን ማሰራጨት መቻሉን ጠቁመዋል።

የገጠር ምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተሠራው ሥራም በቋሚ ቀጥተኛ ድጋፍ 9 ሚሊየን 210 ሺህ 740 ብር ድጋፍ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።

የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በተመለከተም 841 አባላትን ያቀፉ 13 ማኅበራት መደራጀታቸውን ርዕሰ መሥተዳድሩ በሪፖርቱ አመላክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም