ቀጥታ፡

የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ግብዓቶችን 80 በመቶ በሀገር ውስጥ ማሟላት ተችሏል

አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ባለፉት ስድስት ወራት 80 በመቶ ያህሉን የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ግብዓት ከሀገር ውስጥ አቅራቢዎች ማሟላት መቻሉን ገለጸ።


 

የአገልግሎቱ የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ አንዋር አብራር እንዳሉት፤ ጥራታቸውን የጠበቁ የተለያዩ ግብዓቶችን ለሀገር ውስጥ አቅራቢዎች ቅድሚያ በመስጠት እንዲያቀርቡ ተደርጓል።

ይህም መንግሥት የጀመረውን ሀገር-በቀል ኢኮኖሚን ለማበረታታና የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት አገልግሎቱ ከወሰዳቸው እርምጃዎች አንዱ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።


 

በዚህም መሠረት 3 ሺህ 944 የዲስትሪቢዩሽን ትራንስፎርመሮች፣ ከ32 ሺህ በላይ ኢንሱሌተሮች፣ ከ97 ሺህ በላይ የትራንስፎርመር ፕሮቴክሽን ዕቃዎች፣ ከ32 ሺህ ሜትር በላይ ኮንዳክተርና ኬብሎች እንዲሁም ከ201 ሺህ በላይ የተለያዩ የሀርድዌር ዕቃዎች በሀገር ውስጥ አቅርቦት መሸፈኑን አብራርተዋል።


 

አገልግሎቱ ለደንበኞቹ ፈጣን ምላሽ ለመስጠትና የግብዓት አቅርቦት ውስንነትን ለመቅረፍ ሀገር-በቀል አምራቾችን እያበረታታ መሆኑንም አረጋግጠዋል።

የኢዜአ የዲጂታል ሚዲያ ገጾች 👉 https://linktr.ee/ENADigital

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም