በሸገር ከተማ አስተዳደር ከነገ ጀምሮ ለነዋሪው ተንቀሳቃሽ የቤት ለቤት አገልግሎት ይሰጣል - ኢዜአ አማርኛ
በሸገር ከተማ አስተዳደር ከነገ ጀምሮ ለነዋሪው ተንቀሳቃሽ የቤት ለቤት አገልግሎት ይሰጣል
ሸገር፣ የካቲት 4/2018(ኢዜአ):-በሸገር ከተማ ከነገ የካቲት 05 ቀን 2018ዓ.ም ጀምሮ ተንቀሳቃሽ የቤት ለቤት አገልግሎት ለነዋሪው የሚሰጥ መሆኑን የከተማው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አስታወቀ።
የሸገር ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዛሬ ተንቀሳቃሽ የቤት ለቤት አገልግሎቱን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።
መግለጫውን የሰጡት በሸገር ከተማ አስተዳደር የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ስራ አስኪያጅ አቶ መኮንን ሀምቤ እንደገለጹት በከተማው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ወደ ስራ ከገባ ወዲህ ለማህበረሰቡ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ከፍተኛ ውጤት ተገኝቷል።
በከተማው በእስካሁኑ ሂደት ከ32ሺህ 500 በላይ ሰዎች አገልግሎቱን ማግኘት መቻላቸውን ተናግረው፤ በዚህም የማህበረሰቡን እርካታ 99 ከመቶ በላይ ማሳደጉን ገልጸዋል።
አገልግሎቱን ባሉት ክፍለ ከተሞችና ወረዳዎቹ ተደራሽ ለማድረግ ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑንም ተናግረዋል።
ከዚህ የበለጠ ወደ ህዝቡ በመቅረብ ተገልጋዩን ተደራሽ ለማድረግ ከነገ የካቲት 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ተንቀሳቃሽ የቤት ለቤት አገልግሎት ለከተማው ነዋሪ እንደሚሰጥ ስራ አስኪያጁ አስታውቀዋል።
በከተማው የቤት ለቤት አገልግሎቱ በ8 ሴክተሮች 15 ዘርፎችን በጥናት በመለየት ወደ ስራ መገባቱን አንስተዋል።
በዚህም በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመታገዝ ለነዋሪው የመታወቂያ፡ የሞት፣ የጋብቻ፣ የፍቺ፣ የልደትና የስራ አጥነት ካርድ ማደስ፣ መስጠትና ከዚህ ጋር ተያያዥ ጉዳዮች በተሟላ መልኩ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል።
ተንቀሳቃሽ አገልግሎቱ የ2030 ዲጂታል ስትራቴጂን እውን ለማድረግ አጋዥ መሆኑንም አንስተዋል።
አቶ መኮንን እንደተናገሩት አገልግሎቱ ሁሉንም ማህበረሰብ ያማከለ ሲሆን በተለይም አካል ጉዳተኞች፣ አቅመ ደካሞች፣ አዛውቶችና በጤና እክል ወደ ማዕከሉ መምጣት የማይችሉ ዜጎች ጋር የበለጠ ለመድረስ የሚያስችል ነው ብለዋል።
አገልግሎቱ የሚሰጠው በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ፣ በጂፒኤስ፣ ዳታ ሴንተር፣ ካሜራና በሌሎችም በመታገዝ ሲሆን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ክትትልና ቁጥጥርያደርጋልብለዋል።
በተለይም አገልግሎቱ ዘመኑን የዋጀ፣ ተደራሽ፣ አካታችና ውጤታማነት ላይ ያተኮረ መሆኑንና ማህበረሰቡ የመንግስት አገልግሎት ላይ ያለውን እምነት ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም ማህበረሰቡ በቅርበት የሚፈልገውን አገልግሎት በማግኘት ጊዜውንና ጉልበቱን በአግባቡ ለልማት እንዲያውል ለማስቻል ታልሞ ወደ እንቅስቃሴ የተገባ መሆኑን ነው የተናገሩት።