የአዲስ አበባ ስኬታማ የለውጥ እርምጃዎች መዲናዋን ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት ያደረጉ ናቸው - ኢዜአ አማርኛ
የአዲስ አበባ ስኬታማ የለውጥ እርምጃዎች መዲናዋን ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት ያደረጉ ናቸው
አዲስ አበባ፤ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ስኬታማ የለውጥ እርምጃዎች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ መዲናዋን ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት ያደረጉ መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
አሕጉራዊ የተሞክሮ ልውውጥ እና የድርጊት መርሃ-ግብር የሂደት ግምገማ አውደ ጥናት በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ድጋፍ የተካሄደው የአፍሪካ ከተሞች የፋይናንሻል ማኔጅመንት አፈፃጸም የዳሰሳ ጥናት ውጤት በመድረኩ ላይ ይፋ ሆኗል።
በአዲስ አበባ፣ናይሮቢ፣ ዳሬሰላም፣ ሉሳካ፣ ኪጋሊ እና በያውንዴ የአፍሪካ ከተሞች በተካሄደው የዳሰሳ ጥናት ውጤት አዲስ አበባ ከተማ በላቀ አፈፃጸም ቀዳሚ መሆኗ ተገልጿል።
በዳሰሳ ጥናቱ ከተካተቱ ስድስት ዋና ዋና መመዘኛዎች መካከል አዲስ አበባ በአምስት አመላካቾች ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የተሻለ ገቢና የፋይናንስ ሃብት አስተዳደር ስኬታማ ከተማ መሆኗ ተመላክቷል።
በዚሁ ጊዜ የተገኙት የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የመዲናዋን ፈጣን የዕድገት ጉዞ የሚያሳልጡ ስኬታማ የሪፎርም እርምጃዎችን በመውሰድ በቁርጠኝነት መተግበራቸውን ገልጸዋል።
የንግድ ፈቃድ አሰጣጥና የገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱንም በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማዘመንና ግልጸኝነትን በማስፈን በራስ አቅም የልማት ኢንቨስትመንትን የምትደግፍበት ምኅዳር መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል።
የአመራር ቁርጠኝነት፣ ሥራን በዕውቀትና ቴክኖሎጂ መደገፍ እንዲሁም በመንግስትና ህዝብ መካከል ግልጸኝነትን መፍጠር ለከተሞች ትራንስፎርሜሽን መሠረታዊ ጉዳዮች መሆናቸውን አስረድተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ ስትራቴጂክ የሪፎርም እርምጃዎችም የመዲናዋን ሁለንተናዊ ተወዳዳሪነት በማሳደግ ለአፍሪካ ከተሞች ጭምር የለውጥ ተምሳሌት ያደረጉ መሆናቸውን አብራርተዋል።
የከተሞች የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚወሰነው ዛሬ በሚዘረጋ ጠንካራ የፋይናንስ ሥርዓት ነው ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ ለዚህም የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለከተማ የሪፎርም ሥራ የሚያደርገው እገዛ የሚደነቅ ነው ብለዋል።
በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የፆታ፣ የድህነት እና የማህበራዊ ፖሊሲ ዳይሬክተር ዙዛና ብሪክሲዮቫ ሽዊድሮቭስኪ እንዳሉትም የፕሮጀክቱ ዓላማ የማዘጋጃ ቤት የፋይናንስ አቅምን ማጠናከር እና ዘላቂ የፋይናንስ መቋቋም አቅምን ማሳደግ ነው ብለዋል።
ኤኒሼቲቩ ስድስት የአፍሪካ ከተሞችን ማለትም አዲስ አበባ፣ ዳሬሰላም፣ ኪጋሊ፣ ናይሮቢ፣ ሉሳካ እና ያውንዴን እንደሚደግፍም ጠቁመዋል።
የናይሮቢ ከተማ ካውንቲ ምክትል ገዥ ጀምስ ንጆርጅ በበኩላቸው ጉባኤው ለከተሞች እድገት ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው ብለዋል።
በታንዛኒያ የጌሊላ ከተማ ከንቲባ ኖርዲን ቤላል እንዳሉትም ውይይቱ ከተሞች የራሳቸዉን ስራዎች እንዲተገብሩ የሚያደርግ ነዉ ብለዋል።
በመድረኩ የተገኙ የበርካታ አፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላትና ተሳታፊዎችም የአዲስ አበባ ከተማ በልማት ሥራዎች ላይ ያስመዘገበቻቸውን ስኬቶች በተሞክሮነት ተመልክተዋል።