የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል - ኢዜአ አማርኛ
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ በሚደረጉ አራት ጨዋታዎች ይጠናቀቃል።
ምሽት 12 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከሲዳማ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አዳማ ከተማ በሊጉ 14 ጨዋታዎችን አድርጎ በአምስቱ ድል ሲቀናው በሁለቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሰባት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ22 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል።
ሲዳማ ቡና በሊጉ ካከናወናቸው 14 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ሲያሸንፍ የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 18 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ስድስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ሊጉን በ29 ነጥብ እየመራ ነው።
ሁለቱ ቡድኖች በ14ኛ ሳምንት አቻ ከተለያዩባቸው መርሐ-ግብሮች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። አዳማ ከተማ ከሁለት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል።
በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ።
በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 14 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ያሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና በስድስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ14ቱ ጨዋታዎች ላይ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል።
ኢትዮጵያ ቡና በ18 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል።
ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ በ14 ጨዋታዎች ሰባቱን አሸንፎ በአራቱ ሽንፈት አስተናግዶ በሶስቱ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ጎሎች ተቆጥረውበታል።
ሃዋሳ ከተማ በ24 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ሁለቱም ቡድኖች በአሸናፊነት ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ19 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በ18 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፉት ስድስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል።
ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል።
ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከመቻል በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አርባምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። መቻል በ20 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። መቻል ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል።
ጨዋታው አርባምንጭ ከተማ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቻል ወደ ድል መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።