ቀጥታ፡

በኦሮሚያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ27 ማዕከሎች ላይ እየተሰጠ ነው

አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ27 ማዕከሎች ላይ እየተሰጠ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ገለጸ።

መንግስት በተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ በህዝቡ ይነሳ የነበረውን ቅሬታ ለመፍታት በርካታ ውጤታማ ስራዎች እያከናወነ ሲሆን ከእነዚህ መካከል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ይገኝበታል።

በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ወደ ክልሎችም ተስፋፍቶ የመሬት፣ የገቢ እና ሌሎች አገልግሎቶች በአንድ ማዕከል እየተሰጡ መሆኑ ይታወቃል።

የኦሮሚያ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ሃይሉ አዱኛ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ በክልሉ መንግስታዊ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።

በክልሉ በሸገር፣ በአዳማ፣ በቢሾፍቱ፣ በጅማ እና በሻሸመኔ ከተሞች የተጀመረው አገልግሎቱ በዚህ ወቅት ወደ 27 ማዕከሎች ማስፋት መቻሉን ተናግረዋል።


 

አገልግሎቱ በተለይም የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ከመመለስ እና ብልሹ አሰራሮችን ከማስቀረት ጋር በተገናኘ ህዝቡ ለረጅም ጊዜ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል።

ማዕከላቱ በርካታ አገልግሎቶችን በአንድ መስኮት መስጠት ማስቻሉ ብቻ ሳይሆን ተገልጋዩ በአጭር ጊዜ ጉዳዩን እንዲፈጽም እያስቻሉ ነው ብለዋል።

በቀጣይም በተማ አስተዳደር ደረጃ ያሉትን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ወደ ክፍለ ከተሞች የማውረድ ስራ በትኩረት እንደሚከናወንም ተናግረዋል።

በክልሉ በየደረጃው ያለው አመራርም ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር የተያያዙ ችግሮች እንዲቀረፉ ከሌሎች የልማት ስራዎች እኩል ትኩረት ሰጥቶ እየተረባረበ መሆኑን አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም