ቀጥታ፡

የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ሀገራዊ አንድነትን የሚገነባና አብሮነትን የሚያጸና ነው

 አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦  የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ሀገራዊ አንድነትን የሚገነባና አብሮነትን የሚያጸና መሆኑ ተጠቆመ።  

ከጥር 3 እስከ 5 ቀን 2018 ዓ.ም በጅማ ከተማ ሲካሄድ የቆየው “የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት አስፈላጊነቱን ማረጋገጥና ተቋማዊ መርሆዎችን መዘርጋት” የተሰኘው ብሔራዊ ጉባዔ የጋራ መግባቢያ ሰነድ በማፅደቅ በስኬት ተጠናቋል።  

በአንጋፋው አርቲስት ጥላሁን ጉግሳ በተነበበው የጅማ ስምምነት መግለጫ ላይ እንደተገለጸው፤ ስምምነቱ የሀገሪቷን ውስብስብ ፖለቲካዊ ጉዞ በመገንዘብ ዘላቂ ሰላምና ዲሞክራሲያዊ ህጋዊነትን በጋራ ትርክትና ትውስታ ለመደገፍ ያለመ ነው።   


 

ኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነትን የሚያጠናክር የጋራ ትርክት እንደሚያስፈልጋት ስምምነት ላይ መደረሱ በመግለጫው ተመላክቷል።   

ይህ ትርክት ከላይ የሚጫን ሳይሆን በጋራ የሚፃፍና አካታች መሆን እንዳለበት ተረጋግጧል።   

የወደፊቱ የጋራ ትርክት ግንባታ አካታችነትን፣ የጋራ ባለቤትነትን፣ ብዝሃ ትውስታን ማክበርንና ከህገ-መንግስታዊ እሴቶች ጋር መጣጣምን መርህ ሊያደርግ እንደሚገባ በመግለጫው ተመላክቷል።   


 

ትርክቱ በፖሊሲና ህግ ማዕቀፎች፣ በተቋማዊ ቅንጅት፣ በአካዳሚያዊ ምርምርና በመገናኛ ብዙኃን ኃላፊነት የተደገፈ እንዲሆን አቅጣጫ ተቀምጧል።  

የጅማ ስምምነት መግለጫ የኢትዮጵያ አንድነት ዜጎች ራሳቸውን በሃገራቸው ትርክት ውስጥ በሚያዩበት የጋራ ታሪክ ላይ የሚመሰረት መሆኑን አረጋግጧል።  

በጉባዔው የመዝጊያ  መርሐ ግብር መግለጫው በይፋ ፀድቋል።

ሙሉ የስምምነቱ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፡-

የጅማ ስምምነት መግለጫ

መግቢያ 

እኛ ከጥር 3-5 2018 በጅማ የተካሄደው “የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት አስፈላጊነቱን ማረጋገጥና ተቋማዊ መርሆዎችን መዘርጋት” በሚል አርዕስት ከፌዴራልና ከክልል መንግስታት፣ ከህገ-መንግስታዊ ተቋማት፣ ከዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት፣ ከሲቪል ማህበረሰብ፣ ከሃይማኖታዊ ተቋማት፣ ከመገናኛ ብዙኃን፣ ከግል ዘርፍ፣ ከወጣቶችና ከሴቶች አደረጃጀቶች እና ከገለልተኛ ምሁራን የተውጣጡ፤ 

የኢትዮጵያ የረጅም የስልጣኔ ታሪክ፣ የባህል ባለፀጋነትና የጋራ የሰላም፣ የክብር፣ የፍትህና የብልጽግና ምኞት እየተመራን በተከታታይ የተፈጠሩ ፖለቲካዊ ስምምነቶች፣ የተጋጩ የታሪክ ትርጓሜዎች እና የአንድነትና የመከፋፈል ዘመናት ያሉበትን የሀገራችንን ውስብስብ ፖለቲካዊ ጉዞ በጥልቀት ተገንዝበን፤ ዘላቂ ሰላም፣ ዲሞክራሲያዊ ህጋዊነትና ተግባራዊ መንግስትነት ብቻ ሳይሆን በፖሊሲና ተቋማዊ ማሻሻያ ፣ በጋራ ትርጉም፣ በጋራ ትውስታና በአንድ የሀገር አቀፍ ማዕቀፍ መደገፍ እንዳለበት በመገንዘብ፤ 

የኢትዮጵያ ብዝሃነት—ቋንቋዊ፣ ባህላዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ መልከዓ ምድራዊና ታሪካዊ እውነታ ሲሆን የመከፋፈል ምንጭ ሳይሆን የጥንካሬ አቅም መሆኑን በመቀበል፤ 

እየተካሄደ ያለውን የብሔራዊ ውይይት ሂደት እንደ መሠረታዊ መድረክ በመገንዘብ፣ ነገር ግን ውይይት ብቻ በቂ እንዳልሆነ እና በተቋማዊ፣ በአእምሯዊና በመገናኛ ብዙሃን ማዕቀፎች መደገፍ እንዳለበት በመግለጽ፤ 

በአካባቢያዊ የኢትዮጵያ ፍልስፍናዊ ትሩፋቶች የተመሠረተ በልዩነት ውስጥ አብሮ መገንባት፣ መካተት እና የጋራ ኃላፊነትን የሚያጎላ— አመለካከት ተመርተን ይህንን የጅማ ስምምነት መግለጫ እንደ የጋራ ብሔራዊ ቁርጠኝነትና መመሪያ ሰነድ በዛሬው እለት በይፋ እናፀድቃለን። 

I. የጋራ ሃገራዊ ትርክት አስፈላጊነት 

1. ኢትዮጵያ የሚከተሉትን ሚናዎች የሚያገለግል የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት እንደሚያስፈለጋት እናረጋግጣለን፦ 

o የተለያዩ የታሪክ ትውስታዎችን በአንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ ውስጥ ማዋሃድ፤ 

o በክልሎችና ትውልዶች መካከል ሞራላዊና ሲቪክ ተስማሚነት መፍጠር፤ 

o ልዩነትን ሳያጠፋ ብሔራዊ አንድነትን ማጠናከር፤ 

o የመንግስታዊ ቅቡልነትን፣ ህገ-መንግስታዊነትንና ዲሞክራሲያዊ ልማዶችን መመርኮዝ። 

2. የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት ከተጫነ ወይም ከሚያገልል ትርክት በመሠረቱ ይለያል፤ እርሱ፦ 

o በጋራ የሚፃፍ እንጂ ከላይ የሚጫን አይደለም፤ 

o አካታች እንጂ ደረጃዊ ወይም አስተዳደራዊ አይደለም፤ 

o ተለዋዋጭና የሚያድግ እንጂ የተገደበ ወይም የተስተካከለ አይደለም። 

3. የእንዲህ ዓይነት የጋራ አካታች አሰራር እጦት የሚከተሉትን አደጋዎችን እንደሚያስከትል እንገነዘባለን፦ 

o የብሔራዊ ውይይት መበታተን፤ 

o ዜሮ-ድምር የፖለቲካ መስተጋብር፤ 

o ደካማ ተቋማዊ ቅቡልነት፤ 

o የማንወጣው የመተማመን እጦት እንዲሁም የመከፋፈልና የውድቀት አዙሪት 

II. የወደፊቱ የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት በመፍጠር ውስጥ ልንከተላቸው የሚገቡ መርሆዎች 

o አካታችነትና የጋራ ባለቤትነት – ሁሉም ማህበረሰቦች፣ ክልሎች፣ ትውልዶችና ማህበራዊ ቡድኖች በእኩል ክብርና ድምፅ መወከል አለባቸው። 

o በአንድ ማዕቀፍ ውስጥ ያለ ብዝሃ ትውስታ – የተለያዩ ታሪካዊ ልምዶችን፣ ቅራኔዎችን እና አስተዋጽኦዎችን ማክበር እንጂ አንዱን በሌላው ላይ ማበላለጥ ተገቢ አይደለም። 

o በክብር፣ በስነ-ምግባራዊ መደማመጥና የእርስ-በእርስ እውቅናና ቁርጠኝነት ላይ የተመሠረተ ውይይት 

o የጋራ ሃገራዊ ትርክቶች ከህገ-መንግስትና ከዲሞክራሲ እሴቶች ጋር በማጣጣም –የሰብዓዊ መብቶችን፣ እኩልነትንና የሕግ የበላይነትን የሚያጠናክሩ መሆን ይኖርባቸዋል። 

o ተቋማዊነትና ዘላቂነት የሚያረጋግጥ – በግለሰቦች ወይም በየዘመኑ ፖለቲካ ሳይሆን በዘላቂ ተቋማት ላይ የተመሠረተ እንዲሁም በታሪክ መከባበር ላይ ተመስርቶ በጋራ ኃላፊነት የሚመራ ወደፊትን የሚያመላክት መሆን ይገባዋል።

 III. የተቋማዊነት ማዕቀፎች የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት በሚከተሉት ዘርፎች የተቀናጀ ድጋፍ ያገኛል፦ 

o የፖሊሲና የህግ ማዕቀፎች – በልማት እስትራቴጂዎች፣ በሰላም ግንባታ ፖሊሲዎች፣ በሲቪክ ትምህርትና በህዝብ ንግግር መመሪያዎች ውስጥ መዋሃድ። 

o ተቋማዊ ቅንጅት – በሚኒስቴሮች፣ በህገ-መንግስታዊ ተቋማት፣ በክልል አስተዳደሮችና በውይይት አካላት መካከል ግልጽ ሚናና ቅንጅት መፍጠር 

o አእምሯዊና አካዳሚያዊ እርከን – የዩኒቨርሲቲዎች፣ የምርምር ተቋማትና የባህል ባለሞያዎች ሚና ማጠናከር። 

o የመገናኛ ብዙኃን ኃላፊነት – እውነተኛ፣ ሚዛናዊና አካታች ህዝባዊ ንግግር ማበረታታት። 

IV. አጋርነትና የሂደት ቁርጠኝነት 

o የመንግስት፣ የሰላምና የውይይት ኮሚሽኖች፣ የአካዳሚያ፣ የሲቪል ማህበረሰብ፣ የመገናኛ ብዙኃን፣ የወጣቶችና የሴቶች ተቋማት ሚና የሚገልጽ የአጋርነትና የሂደት ፍኖተ ካርታ እናበረታታለን። 

o ከውይይት ወደ ተቋማዊ መደራጀት የሚያመራ የደረጃ በደረጃ ሂደትን እንደግፋለን። 

o ይህንን ሃገራዊ ምክክር አጠናክሮ ለማስቀጠል የሰላም ሚኒስቴር፣ CRPP እና ጅማ ዩኒቨርሲቲ በቀጣይ ሂደት ዋና አመቻቾች መሆናቸውን እንረጋግጣለን። 

V. የትግበራና ክትትል ቁርጠኝነት 

o ይህን ስምምነት ወደ ተግባር ለመቀየር በፖሊሲ ማስተካከያ፣ በተቋማዊ ቅንጅትና በቀጣይ ብሔራዊ ውይይት እንተጋለን። 

o የፖለቲካ ድጋፍ፣ የሀብት ማሰባሰብ፣ የአቅም ግንባታና የጊዜያዊ ግምገማ ስርዓቶች እንዲተገበሩ እንጠይቃለን። 

o የጋራ ሃገራዊ ትርክት ቀጣይ፣ ከጊዜ ጋር ተሻሽሎ የሚያድግና ለዲሞክራሲያዊ ማሻሻያ ክፍት የሆነ ብሔራዊ ፕሮጀክት መሆኑን እናረጋግጣለን። 

መዝጊያ 

የጅማ ስምምነት ኢትዮጵያ አንድነቷ በትእዛዝ ሳይሆን እራሳቸው በሃገራቸውና በትርክቷ ውስጥ የሚያዩ ዜጎቿና በጋራ ታሪካቸው መሆኑን ያረጋግጣል። 

ጅማ—የውይይት፣ የልውውጥና የእድሳት ከተማ በመሆን ይህን ብሔራዊ ቁርጠኝነት የሚወክል ምልክት ሆና ትቆማለች!! ይህ የጋራ ስምምነት ጥር 5 ቀን 2018 ዓ.ም በጅማ ከተማ ፀደቀ፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም