ቀጥታ፡

የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች እየተመዘገቡ ነው

አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 በጀት ዓመት ባለፉት ስድስት ወራት የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች መመዝገባቸውን የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ።

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት የበጀት ዓመቱን ያለፉት ስድስት ወራት የልማት አፈፃጸም አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል።

መግለጫውን የሰጡት የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ኃላፊ ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ፥ 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዓመት ነው ብለዋል።

በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራትም የኢትዮጵያን ማንሰራራት የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል።

በዚህም በብዝኅ የኢኮኖሚ ዘርፍ በ2030 ኢትዮጵያን አፍሪካዊት የብልጽግና ተምሳሌት የሚያደርጉ የልማት ስኬቶች እየተመዘገቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ምርቃት የጉባ ብስራት ፕሮጀክቶች ጅማሮም ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ ማጠናቀቅ እንደምትችል የሚያሳዩ መሆናቸውን አብራርተዋል።

ኢትዮጵያን የወደፊቷ የአፍሪካና የዓለም የአየር ትራንስፖርት ፋና ወጊ በማድረግ 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ያለው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማሪፊያ ግንባታ መጀመር የንግድ ትስስርን ለማሳለጥ ጉልህ ጠቀሜታ እንደሚኖረው በአብነት ጠቅሰዋል።

የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም በሁሉም መስኮች ችግሮችን በማረም የኢትዮጵያን ዕድገት የሚያሳልጥ ውጤት መመዝገቡን አብራርተዋል።

በዚህም በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና ዲጂታል ብዝኅ የኢኮኖሚ መስኮች እመርታዊ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

የመደመር መንግሥት እሳቤ በግብርና መስክ በበጋ መስኖ ስንዴ፣ በኩታ ገጠምና በሌማት ትሩፋት የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ተመጽዋችነትን የሚገታ የምርት ውጤት እየተገኘ መሆኑን አንስተዋል።

የጉባ ብስራት ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅም ጠንካራ ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግ ጠቅሰዋል።

ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል ለማድረግ በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማትም በበርካታ ከተሞች በስፋት እየተሰራበት መሆኑን ገልጸዋል።

በዲፕሎማሲ መስክም በአሕጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መድረኮች የኢትዮጵያ ተሳትፎም ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ የአፍሪካ ድምጽ መሆን ያስቻለ ስኬት መመዝገቡን ተናግረዋል።

በመንግስትና ሕዝብ መካከል የተደረጉ መድረኮችም ኢትዮጵያ ያስመዘገበችው የልማት ስኬት ዕውቅና የተሰጠበት መሆኑን አብራርተዋል።

በዚህ ዓመት የሚካሄዱት የሀገራዊ ምክክርና ሀገራዊ ምርጫ ዐበይትና ወሳኝ ሁነቶችን በአሳታፊነት፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ መንገድ በስኬት ለማስኬድም መንግስት በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም