ኢትዮጵያ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ቁርጠኛ ነች - ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ቁርጠኛ ነች - ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር)
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ቁርጠኛ ነች ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ገለጹ።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ከቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ጋር ተወያይተዋል።
በውይይታቸውም ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያላትን ጠንካራ እና በሁኔታዎች የማይቀየር ስትራቴጂካዊ አጋርነት አንስተዋል።
ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት የረዥም ጊዜ ወዳጅነት፣ ትብብር እና በጋራ መከባበር ላይ የተመሠረተ መሆኑንም ገልጸዋል።
ቻይና ለኢትዮጵያ ልማት እያደረገች ያለውን ድጋፍ አድንቀው ኢትዮጵያ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።
ቻይና ያቀረበችውን የአፍሪካ ቀንድ የሰላምና ልማት ኢኒሼቲቭ ትኩረት በመስጠት በቀጣናው ያሉ የደኀንነት፣ የልማትና አስተዳደር ተግዳሮቶችን ለመፍታት ያለውን ጠቀሜታ ማንሳታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።
ኢትዮጵያ የኢትዮ-ቻይና አጋርነትን በተለያዩ ባለብዙ መድረኮች ማለትም በአንድ ቀበቶና መንገድ ኢኒሼቲቭ፣ በቻይና-አፍሪካ ትብብር መድረክ፣ ብሪክስ-ፕላስ እና በተባበሩት መንግሥታት ማዕቀፎች ጨምሮ በትብብር ለመሥራት ቁርጠኛ መሆኗንም አረጋግጠዋል።
የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ በበኩላቸው ወደ አፍሪካ ያደረጉት ጉብኝት በጎርጎሮሳውያኑ 2026 የመጀመሪያው ወደ ውጭ ያደረጉት ጉዟቸው መሆኑን ጠቁመው ኢትዮጵያ የመጀመሪያ መድረሻቸው መሆኑን ገልጸዋል።
ይህም ቻይና ከአፍሪካ ጋር ያላትን ዘላቂ አጋርነት እና ኢትዮጵያ ደግሞ ዋነኛ ስትራቴጂካዊ አጋር መሆኗን እንደሚያሳይ ተናግረዋል።
ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሁሉንም ዓይነት አጋርነት በተለያዩ የትብብር ዘርፎች የበለጠ ለማጠናከር ያላትን ቁርጠኝነትም ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል።
ሁለቱ ሚኒስትሮች በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና በባለብዙ ወገን የግንኙነት መድረኮች ላይ ስትራቴጂካዊ ቅንጅትን ለማጠናከር ተስማምተዋል።