በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት መሠረት ዕሴት የታከለበት ቡናን መላክ ተጀምሯል - ኢዜአ አማርኛ
በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት መሠረት ዕሴት የታከለበት ቡናን መላክ ተጀምሯል
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት መሠረት ዕሴት የታከለበት የኢትዮጵያ ቡናን ለአፍሪካ ሀገራት ገበያ መላክ መጀመሩን የኢትዮጵያ ቡና እና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ።
የአፍሪካ ሕብረት መረጃ እንደሚያሳየው የአፍሪካ ሀገራት 85 በመቶ ምርታቸውን ለአውሮፓ፣ እስያ፣ ሰሜንና ላቲን አሜሪካ ገበያ የሚልኩ ሲሆን በአንፃሩ የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጣቸው ከ15 በመቶ ያልበለጠ ነው።
የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት ትግበራም የሀገራቱን የእርስ በእርስ የንግድ ትስስር በማሳለጥ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብና ኢኮኖሚያዊ ትስስርን እንደሚያሳድግ ታምኖበታል።
አህጉራዊ የነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቱም የአፍሪካ ሀገራትን የንግድ ታሪፍና መሰናክል በማስወገድ ወጥ በሆነ የአሰራር ሥርዓት የእርስ በእርስ የገበያ ትስስርን ማሳለጥ ዋና ዓላማው ያደረገ ነው።
ይህም የአህጉሪቷን አባል ሀገራት የንግድ ልውውጥ በማሳደግ፣ የኢንዱስትሪ ዕድገትን በማፋጠንና ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር የአፍሪካን ኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ለማሳለጥ ከፍተኛ ፋይዳ አለው።
በዚህም ኢትዮጵያ በአህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቱ መሰረት ከመስከረም 29 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ገበያ የንግድ ምርቶችን መላክ ጀምራለች።
የኢትዮጵያ ቡና እና ሻይ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሻፊ ዑመር ለኢዜአ እንዳሉት፤ በአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣና ሥምምነት መሰረት የኢትዮጵያ ቡና ገበያ መዳረሻን ለማስፋት እየተሰራ ነው ።
የአፍሪካን ሰፊ የገበያ ዕድል ለመጠቀም የኢትዮጵያን ጥሬ ቡና ከመላክ ይልቅ ዕሴት ጨምሮ ማቅረብ ወሳኝ መሆኑንም ገልጸዋል።
በዚህም በአንዳንድ የአፍሪካ ሀገራት ዕሴት የተጨመረበት ቡናን የመላክ ጅማሮ የበለጠ ለማስፋት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ አዳዲስ የቡና ገበያ መዳረሻዎችን እያሰፋች ነው ያሉት አቶ ሻፊ፤ ለአብነትም በ2016 ዓ.ም 64 ሀገራት የነበረውን የኢትዮጵያን የቡና ገበያ መዳረሻ በ2017 ዓ.ም ወደ 84 ማሳደግ ተችሏል ብለዋል።
የኢትዮጵያን ነባር የቡና ገበያ መዳረሻ በማጠናከርና አዳዲስ ገበያን ለማስፋት በተለያዩ ሀገራት ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ቻይናን ጨምሮ አስር የእስያ ሀገራት የኢትዮጵያን ቡና እየገዙ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በቀጣይም ቡና ላይ ዕሴት በመጨመር የአፍሪካና እስያ ገበያን ለመጠቀም ከኢትዮጵያ ቡና ላኪዎችና የአውሮፓ ባለሃብቶች ጋር በመቀናጀት ዕሴትን ጨምሮ መላክ ላይ እንዲሳተፉ ይሰራል ብለዋል።