ቀጥታ፡

የኮሪደር ልማት ስራው የነዋሪው የልማት ተነሳሽነት እንዲጎለብት አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው

ጎንደር ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦የጎንደር ከተማ የኮሪደር ልማት ስራ ለከተማዋ ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል ከመፍጠር ባሻገር የነዋሪው  የልማት ተነሳሽነት እንዲጎለብት አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ፡፡

የጎንደር ከተማ ሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ስራ አካል የኮንክሪት አስፓልት መንገድ ግንባታ እየተፋጠነ መሆኑ እና በመጪው የጥምቀት በዓል በይፋ ተመርቆ ስራ እንደሚጀምር ታውቋል፡፡


 

የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በከተማዋ የሚከናወነው ሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ስራ የህዝቡን ተሳትፎ በማቀናጀት የከተማዋን ገጽታ ለመቀየርና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን በሚያሳልጥ መልኩ እየተካሄደ ነው፡፡


 

የሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማቱ የእግረኞችና የብስክሌት መንገዶችን ጨምሮ ዘመናዊ መናፈሻዎችና ፓርኮችን እንዲሁም አረንጓዴ ስፍራዎችን በማካተት መገንባቱን አስረድተዋል፡፡

የዚሁ ስራ አካል የሆነው የኮንክሪት አስፓልት  8 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታን በማፋጠን ለጥምቀት በዓል በማጠናቀቅ ለትራፊክ ክፍት ለማድረግ ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ 


 

በተጨማሪም ኮሪደሩ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን፣ ዘመናዊ የመንገድ ዳር መብራቶችንና ስማርት የመጸዳጃ ቤቶችን ያካተተ ሲሆን ከተማዋ የዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ  እንድትሆን ምቹ ሁኔታን የፈጠረ ነው ብለዋል፡፡

የኮሪደር ልማት ስራው ለከተማው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፍጠሩን ጠቁመው በህዝቡ ዘንድም የልማት ተነሳሽነት እንዲጎለብት የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል፡፡

ሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ስራ 12 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትርን የሸፈነ ሲሆን በመጪው ጥር ወር  በታላቅ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ስርዓት በሚከበረው የጥምቀት በዓል በይፋ ተመርቆ ስራ እንደሚጀምር ገልጸዋል፡፡


 

የከተማውን  የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ይበልጥ በማነቃቃት በኩል የኮሪደር ልማት ስራው ትልቅ ተስፋን የሰነቀና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውም የጎላ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ከፍተኛ ወጪ ተደርጎባቸው የተገነቡት ግዙፍ መሰረተ ልማቶች ለህዝቡ የዘመናት የመልማት ጥያቄ ምላሽ በመስጠት የከተማዋን ዳግም ትንሳኤ ያበሰሩ ታላላቅ የልማት ፕሮጀክቶች ናቸው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም