ኢትዮጵያ እና ኦማን በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ እና ኦማን በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ኦማን የአፍሪካ ቀንድን ጨምሮ በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር በትብብር እንደሚሰሩ አስታወቁ።
የመጀመሪያው የኢትዮጵያ እና የኦማን የፖለቲካ ምክክር በአዲስ አበባ ተካሄዷል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ ኢትዮጵያ እና ኦማን ኢኮኖሚና ኢንቨስትመንትን ጨምሮ ሀገራቱ የሁለትዮሽ ትስስራቸውን ማጠናከር የሚችሉባቸው በርካታ ዘርፎች እንዳሉ በምክክሩ ላይ መነሳቱን የፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ ዘገባ ያመለክታል።
ቱሪዝም እና የሀገራቱ ዜጎች የጉብኝት ልውውጥ የሀገራቱን ትብብር ለማጎልበት እንደሚያስችል ተናግረዋል።
ሀገራቱ በአፍሪካ ቀንድ እና የባህረ ሰላጤው ቀጣና ጉዳይ ላይ ያላቸውን ግንነት ለማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ በስፋት መምከራቸውን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ እና ኦማን ተከታታይ የሁለትዮሽ ውይይቶችን ለማድረግ እንዲሁም በቱሪዝም እና ንግድ ዘርፍ ያላቸውን ትስስር ለማሳደግ ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን ነው ሚኒስትር ዴኤታው የጠቆሙት።
የኦማን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሼህ ከሊፋ ቢን አሊ አል ሃርቲ በኢትዮጵያ ያደረጉት የስራ ጉብኝት አላማ የሁለቱን ሀገራት የሁለትዮሽ እና ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር መሆኑን ለፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ ገልጸዋል።
በጉብኝቱ ኦማን እና ኢትዮጵያ በሁለትዮሽ እና በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ትብብራቸውን ለማጠናከር እንደተስማሙ ተናግረዋል።
ስምምነት ከተደረሰባቸው ጉዳዮች መካከል የአፍሪካ ቀንድ እና ባህረ ሰላጤ ቀጣና ላይ በጋራ መስራት እንደሚገኝበት ተናግረዋል።
ኦማን ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር ለማጠናከር ቁርጠኛ እንደሆነችም አረጋግጠዋል።
ሁለቱ ወገኖች የሁለትዮሽ የፖለቲካ ምክክር በማድረግ የሁለትዮሽ ትብብርን ለማሳደግ ፣በቀጣናዊ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ ቅንጅትን ለማጠናከር የጋራ የመግባቢያ ስምምነት በምክክሩ ወቅት ተፈራርመዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፖለቲካ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ ሼክ ካሊፋ ቢን አሊ አል ሀርቲ ከውጭ ጉደይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ጋር የሁለት ሀገራት ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ እና በጋራ ቀጣናዊና የሰላም እንዲሁም የጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል ።