ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መረጋገጥ የላቀ ሚና ይጫወታል - ኢዜአ አማርኛ
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መረጋገጥ የላቀ ሚና ይጫወታል
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ይበልጥ መረጋገጥ የላቀ ሚና እንደሚጫወት የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ገለጹ፡፡
የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ፤ ጥራት ያለውና ፍትሐዊ የትምህርት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂን አማራጮች በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡
ዓለም አቀፋዊውን የዕድገት ፍጥነት ተከትሎ በትምህርት መስኩ ዕውቀትና ክህሎቱ የዳበረ ማኅበረሰብን ለመፍጠር ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ጉልህ አሻራ አሳርፏል ነው ያሉት።
በተለይም የመማር ማስተማር ሂደቱን በማዘመንና የፈተና አሰጣጥ ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ በማድረግ የፈተና ደኅንነት እንዲጠበቅ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡
ስትራቴጂው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሀገሪቱን የዲጂታላይዜሽን ጉዞ የሚደግፉ የሥልጠና መስኮችን እንዲከፍቱና በዘርፉ ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት የሚያስችሉ ግብዓቶች እንዲሟሉ ምቹ መደላድል መፍጠሩንም አክለዋል።
መንግሥት የሀገሪቱን ብልጽግና ለማረጋገጥ የጀመረውን የማዘመን ሥራ ይበልጥ ለማሳለጥ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ተግባራዊ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡
ይህ ስትራቴጂ ዜጎች በዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮች ታግዘው ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲማሩ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።
ስትራቴጂው የትምህርት ተደራሽነትን ከጥራት ጋር በማጣመር ረገድም የላቀ ፋይዳ እንደሚኖረው ጠቁመዋል፡፡
በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ከኢንዱስትሪው ጋር ይበልጥ ለማቀራረብ በትኩረት ይሠራል ብለዋል፡፡
ይህም ተማሪዎች በቴክኖሎጂው ረገድ ተግባር ተኮር ዕውቀትና ክህሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል።
በተጨማሪም በዲጂታላይዜሽን ዙሪያ የሚከናወኑ የምርምር ውጤቶች ለተግባራዊ ጥቅም እንዲውሉ በማድረግ የትምህርት ዘርፉ ለስትራቴጂው ስኬት የሚጠበቅበትን ሀገራዊ ኃላፊነት እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።