በመዲናዋ እየተከናወኑ ያሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ተግባራት ለወጣቶች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በመዲናዋ እየተከናወኑ ያሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ተግባራት ለወጣቶች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ተግባራት ለወጣቶች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ “የኢንተርፕራይዞች ውጤታማነት ለአዲስ ብልፅግና’’ በሚል መሪ ሀሳብ ሲያካሂድ የቆየው የነባር ኢንተርፕራይዞች ንቅናቄ ማጠቃለያ መድረክ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ነው፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት፤ ወጣቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው።
በየዓመቱ አዳዲስ ሥራ ፈላጊ ወጣቶች የአጭርና የረጅም ጊዜ ሥልጠናዎችን ወስደው ወደ ሥራ እንዲሰማሩ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህም ወጣቶቹ በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ዕድል ፈጥሮላቸዋል ብለዋል።
ነባር ኢንተርፕራይዞችም ተከታታይ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው ወደ ተሻለ የዕድገት ደረጃ እንዲሸጋገሩ እየተደረገ መሆኑን ኃላፊው ጠቁመዋል።
በአጠቃላይ ወጣቶችን ተጠቃሚ ለማድረግ በከተማው እየተፈጠሩ ያሉ የሥራ ዕድሎች ውጤታማ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
በመድረኩ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ከሁሉም ክፍለ ከተሞች የተወጣጡ የኢንተርፕራይዝ አባላት ተገኝተዋል።