ኢንስቲትዩቱ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት አሳድጓል - ኢዜአ አማርኛ
ኢንስቲትዩቱ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት አሳድጓል
ወልቂጤ ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ የባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ እና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ገለጸ።
ኢንስቲትዩቱ የእንሰት መፋቂያና ማቀነባበሪያ ማሸን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ በሰስየ ቀበሌ ለሚገኙና በማህበር ለተደራጁ አርሶ አደሮች አስረክቧል።
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የማህበረሰቡን ኑሮና የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ የሚያቀሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያፈለቀ እና እያበለጸገ ይገኛል።
ከዚህ ቀደምም የአቮካዶ ዘይት መጭመቂያ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለሲዳማ ክልልና ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል እንዲሁም የበቆሎ መሸልቀቂያ ማሽን ለምስራቅ ጉራጌ ዞን ተጠቃሚዎች ማስተላለፉን ተናግረዋል።
አሁን ላይ ጥራቱን የጠበቀ የእንሰት መፋቂያና ማብላያ ማሽን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ በማህበር ለተደራጁ 15 ወጣቶች ማቅረብ ችሏል ነው ያሉት።
ማሽኑ የጊዜና የጉልበት ብክነትን በመቀነስ የቆጮ እና ቡላ ማብላያ ሂደትን ከማሳጠር ባለፈ የተሻለ ምርት የሚያስገኝ መሆኑን ገልጸዋል።
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሳይንስ፣ ኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰላሙ አማዶ፣ ከእንሰት ምርት ምግብ በማዘጋጀቱ ሂደት የሴቶች ጫና ይበዛ እንደነበር ጠቅሰው ማሽኑ ወንዶች ጭምር በስራው እንዲሳተፉ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በዚህ ማሽን ከቆጮና ቡላ ባለፈ ሌሎች ምግቦችን ማዘጋጀት እንደሚቻል አመልክተው፤ ማሽኑ ለብዙዎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል።
ማሽኑን በክልሉ እንሰት አምራች አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።
የእንሰት ሰብል ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን በማሳደግ የአምራቹን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ያሉት ደግሞ የጉራጌ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ ናቸው።
ችግር ፈቺ የሆነ የእንሰት መፋቂያ እና በአጭር ጊዜ ያለ ብክነት ወደ ምርት የሚቀይሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለህብረተሰቡ ተደራሽ እንዲሆኑም አስተዳደሩ ድርሻውን ይወጣል ብለዋል።
በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አዲሱ ምስጎ፤ የተሰጣቸው ማሽን የእንሰት መፋቂያ፣ የአሚቾ ማድቀቂያ እና የቡላ መጭመቂያ መሆኑን ተናግረዋል።
ማሽኑ በቀን አስከ 40 እንሰት መፋቅ የሚያስችል ሲሆን ይህም ተጠቃሚነታቸውን የበለጠ የሚያሳድግ መሆኑን ጠቁመዋል።
ወይዘሮ ይስሬሽ ሰክት በበኩላቸው ማሽኑ እንሰት ፍቆ ለምግብነት ለማዋል የሚባክነውን ጊዜ እና ጉልበት የሚቀንስ መሆኑንም አንስተዋል።