የመደመር መንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ ላይ አይተኬ ሚና እንዳላቸው በጽኑ ያምናል - ኢዜአ አማርኛ
የመደመር መንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ ላይ አይተኬ ሚና እንዳላቸው በጽኑ ያምናል
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ የመደመር መንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ ላይ አይተኬ ሚና እንዳላቸው በጽኑ እንደሚያምን እና ለተግባራዊነቱም እየሰራ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ሀሳብ የለውጥ ኃይል ነው። ምሁራን ደግሞ የለውጥ ወኪሎች ናቸው ብለዋል።
ምሁራን በማኀበረሰብ ውስጥ የሚፈጥሩት ለውጥም ሀገርን ወደ ብልጽግና እንደሚወስድ ጠቅሰው በዚህ ረገድም ምሁራን ሀሳብ አክባሪና አፍቃሪ፣ ጥልቅ አሰላሳይ፣ አንባቢ፣ ችግር ፈቺና መፍትሄ አሳሽ መሆን እንደሚጠበቅባቸው አመልክተዋል።
በዛሬው እለት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በማስመልከት ዩኒቨርሲቲው ባዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ጽሁፍ በማቅረብ መሳተፋቸውን ጠቁመዋል።
በመድረኩም የኢትዮጵያ ምሁራን በሁለንተናዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ሚና በሚመለከት ሰፊ ውይይት መደረጉን ተናግረዋል።
የመደመር መንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ ላይ አይተኬ ሚና እንዳላቸው በጽኑ ያምናል፣ ለተግባራዊነቱም እየሰራ ይገኛል ነው ያሉት።
ተቋማቱም የመማር ማስተማር እንዲሁም የምርምር ስራዎችን ከቴክኖሎጂ ጋር በማናበብ ወደ ፈጠራና ተግባር መለወጥ እንደሚጠበቅባቸው አሳስበው ይህም የኢትዮጵያን ብልጽግና በተደመረ አቅም ለማፋጠን ሚናው ከፍተኛ ነው ብለዋል።