የፖሊስ ተቋማት ተልዕኳቸውን በብቃት መወጣት እንዲችሉ አስፈላጊውን ግብዓት የማሟላት ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል - ኢዜአ አማርኛ
የፖሊስ ተቋማት ተልዕኳቸውን በብቃት መወጣት እንዲችሉ አስፈላጊውን ግብዓት የማሟላት ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦የፖሊስ ተቋማት ተልዕኳቸውን በብቃት መወጣት እንዲችሉ አስፈላጊውን ግብዓትና መሰረተ-ልማት የማሟላት ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአዲስ አበባ የተገነቡ 32 አዳዲስ የፖሊስ እና የእሳትና አደጋ ሥጋት መከላከያ ተቋማትን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል፡፡
እነዚህ ፕሮጀክቶች የከተማዋን ሰላምና ጸጥታ ይበልጥ ለማጠናከር በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተገነቡ የክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያዎች፣ የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ ማዕከላት፣ ፖሊስ ጣቢያዎች፣ የፖሊስ ካምፖች እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤቶች ናቸው።
የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ ነው።
እነዚህ ተግባራት የከተማዋን ሰላምና ጸጥታ ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችሉ እንደሆኑም ተናግረዋል።
በዛሬው ዕለት ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት ፕሮጀክቶች ፖሊስ ከህዝቡ ጋር በቅርበት በመሆን ወንጀልን አስቀድሞ ለመከላከልና አደጋን ለመቀነስ እና ለመቆጣጠር የሚያስችሉ እንደሆነ ገልፀዋል።
እንዲሁም የፖሊስን አገልግሎት ተደራሽነት ከማሳደግ ባለፈ የጸጥታ አካላት በሙሉ አቅማቸው እንዲሰሩ ለማስቻል የተከናወኑ መሆናቸውን ከንቲባዋ ገልጸዋል።
አዲስ አበባን እንደ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መዲናነቷ ለነዋሪዎቿና ለጎብኚዎቿ ምቹ የማድረግ ተግባር መሆኑን ጠቅሰዋል።
ሰላም ለሁሉም ነገር መሠረት ነው ያሉት ከንቲባዋ በዚህም የጸጥታ መዋቅርን በቴክኖሎጂና በሰው ኃይል የማዘመን ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።