የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን አጠቃላይ እንቅስቃሴን የሚያሳይ ድረ-ገጽ ይፋ ሆነ - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን አጠቃላይ እንቅስቃሴን የሚያሳይ ድረ-ገጽ ይፋ ሆነ
አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 15/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን አጠቃላይ እንቅስቃሴን የሚያሳይ ድረ ገጽ ይፋ ሆኗል።
የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን የዝግጅትን በ etaf90years.com ድረ-ገፅ አማካኝነት አጠቃላይ መረጃ ማግኘት እንደሚቻል ተቋሙ አስታውቋል።
የምስረታ ቀን በዓሉ ላይ ኅብረተሰቡ እንዲሳተፍም የኢትዮጵያ አየር ኃይል ባወጣው መግለጫ ገልጿል።
የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን በዓሉን አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል:-
ነሐሴ 12 ቀን 1921 ዓ.ም የአቪዬሽን ቴክኖሎጂ ወደ ኢትዮጵያ የገባ ቢሆንም አየር ኃይላችን እንደ ተቋም አደረጃጀት ይዞ በይፋ የተመሰረተው ሕዳር 20 ቀን 1928 ዓ.ም ኢትዮጵያዊው ሻለቃ ሚሽካ ባብቼፍ የአየር ኃይል አዛዥ ሆነው በተመደቡበት ቀን ነው፡፡
ጀግናው የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90 ዓመታትን ባስቆጠረው የምስረታ ታሪኩ በየዘመናቱ ሁሉ የሀገርን ሉዓላዊነት በመጠበቅ አኩሪ ታሪክ ያለው ስመ ገናና ተቋም ነው፡፡አየር ኃይላችን የኢትዮጵያን የአየር ክልል በጀግንነት ከመጠበቅ ባሻገር በዓለም አቀፍ የሠላም ማስከበር ተልዕኮዎች በመሰማራት የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርጎ አውለብልቧል፡፡
የሠላም አምባሳደርነቱንም በተግባር አሳይቷል፡፡ በድል እና በመስዋዕትነት የደመቀ ታሪክም አኑሯል፡፡ በስልጠናው ዘርፍም ከራሱ አልፎ የሌሎች ሀገራት የአየር ኃይል ሙያተኞችን ማሰልጠኑን ኢቢሲ ዘግቧል፡፡
90ኛ ዓመት የአየር ኃይል የምስረታ ቀን በዓል "የኢትዮጵያ አየር ኃይል የነፃነትና የአንድነት ምልክት" በሚል ዋና መሪ ቃል ከጥር 15 ቀን 2018 ዓ.ም እስከ ጥር 19 ቀን 2018 ዓ.ም ድርስ በተለያዩ መርሃ ግብሮች በድምቀት ይከበራል፡፡
የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች ማክበር የጀመረ ሲሆን የዚሁ አካል የሆነውና "ለአየር ኃይል እድገት በሙሉ አቅሜ እሮጣለሁ" በሚል መሪ ቃል ሕዳር 21 ቀን 2018 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ ዓለም አቀፍ የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር በድምቀት ተካሂዷል፡፡
የአየር ሀይል የተመሰረተበት 90ኛ አመት ምክንያት በማድረግ ከፍተኛ ዝግጅት የተደረገበት የአየር ላይ ትርኢት ይካሄዳል-ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ
የኢትዮጵያን ታላቅነት የሚመጥን ታላቅ አየር ኃይል እየተገነባ ነው -ሌ/ጄኔራል ይልማ መርዳሳ
ይህ የሩጫ ውድድር ህብረተሰቡ በከፍተኛ መነቃቃት የተሳተፈበት፣ ተቋሙና ህዝቡ የተሳሰረበት፣የቱሪስት መዳረሻ የሆነችው ቢሾፍቱ ከተማ የተዋወቀችበት ከመሆኑም ባሻገር በቀጣይ ለሚካሄዱት ኩነቶች የአየር ኃይል የምስረታ ቀን ዋናው በዓል መሰረት ጥሎ ያለፈ ታሪካዊ ውድድር ነው፡፡
በመቀጠል ከጥር 15 እስከ ጥር 19 ዓ.ም ጀምሮ የሚኖረው የሚከተሉትን ኩነቶች የያዘ ነው የመጀመሪያው በዓይነቱ ለየት ያለ እና ለሁለተኛ ጊዜ በኢትዮጵያ አየር ኃይል አዘጋጅነት ‘የአንበሶች ሠማይ! ኢትዮጵያ’ በሚል መሪ ቃል የኢትዮጵያ አየር ኃይል፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የአየር ኃይል፣ የሩሽያ የአየር ኃይል ትርኢት ቡድን፣ የሞሮኮ የአየር ኃይል እና የቼክ ሪፐብሊክ አየር ኃይል በጋራ የጥቁር አንበሳ የአየር ትርኢት 2026 በድምቀት የሚካሄድ ይሆናል፡፡
በመቀጠል በከፍተኛ ጉጉት የሚጠበቀው "የወደፊቱን የአቪዬሽን አቅም በጋራ እንገንባ" በሚል መሪ ቃል የኢትዮጵያ አየር ኃይል፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የቻይና፣ የህንድ የአሜሪካ እና የደቡብ አፍሪካ ታላላቅ ኩባንያዎች ብሎም ከ 25 በላይ የሚሆኑ በአቪዬሽን ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገራት የአቪዬሽንና የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የሚሳተፉበት ስታቲክ ዲስፕለይ እና የአቪዬሽን ቴክኖሎጂ ኤክስፖ2026 ይካሄዳል፡፡
የኢፌዴሪ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን በዓል ከሚያከናውናቸው ኩነቶች አንዱ ከ38 በላይ የአፍሪካ ሀገራት የአየር ኃይል አዛዦች የሚሳተፉበት እና "የጋራ ስራዎቻችንን አጠናክረን የተረጋጋ ዓለም እንገንባ" በሚል መሪ ሀሳብ ለ3ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ አየር ኃይል አዘጋጅነት ፊውቸር አፍሪካ አየር ኃይሎች ፎረም ታላላቅ የአቪዬሽን ባለሙያዎች በተገኙበት የሚካሄድ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያ ከአቪዬሽን ቴክኖሎጂ ጋር ያላትን ቅርብ ትስስር በተግባር የሚያረጋግጥ ይሆናል፡፡
አየር ኃይል የሀገርን ሉዓላዊነት በማስከበር አኩሪ ታሪክ አለው- ሌ/ጄኔራል ይልማ መርዳሳ
ኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን በዓል ከሚካሄዱ መርሃ ግብሮች መካከል የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ የጦር አዛዦች እንዲሁም የሀገራችን ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት "ሀገርን በማገልገል የሚገኝን ክብር መዘከር" በሚል መሪ ቃል ከህብረተሰቡ ጋር በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ሕዝባዊ ውይይት የሚደረግ ይሆናል፡፡
የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን አጠቃላይ የበዓሉን የአከባበርን ሁኔታ የሚገልፅ እና የአየር ኃይልን ታሪክ የበለጠ የሚያሳውቅ፣ የዝግጅቱን ዝርዝር የሚያሳይ እንዲሁም የባለፉት ዓመታትን የተቋሙን የለውጥ ሂደት የሚያስቃኝና etaf90years.com የተሰኘ የኢቨንት ድረ ገፅ ያለው ሲሆን በዚሁ ድህረ ገፅ ሁሉንም የበዓሉ ኩነቶች ማግኘት የመግቢያ ቲኬት መግዛትና በድረ ገፅ ኩነቶቹን መከታተል ይቻላል፡፡
የኢትዮጵያ አየር ኃይል በ90 ዓመት ጉዞው ለኢትዮጵያችን መስዋዕትነት ከፍሏል፡፡ የኢትዮጵያን የአየር ክልል በጀግንነት ጠብቋል፡፡ ሀገር አፅንቷል፤ ሀገር አሻግሯል፡፡ በእሳት ተፈትነው ያለፉ ብዙ ጀግኖችንም አፍርቷል፡፡
በውጊያ መሰረተ ልማት፣በሰው ኃይል ግንባታና ትጥቅ በማሟላት ኢትዮጵያን የሚመጥን ተቋም እየተገነባ ነው
የከበረ እና የገዘፈ ታሪክ ያለው የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ ቀን በዓሉን ሲያከብርም ያለፈውን ለመዘከር አሁናዊ የተቋሙን ቁመና ለማቀብ፣ የደረሰበትን ሁሉን አቀፍ ዝግጁነት ለማሳየት፣ የሀገራችንን ገጽታ በማጉላት እና የኢትዮጵያን የአቪዬሽን ተስፋ ለማነሳሳት በሚያስችሉ ዝግጅቶች እንዲሁም ተግባራት የሚከበር መሆኑ ተመላክቷል።
ኅብረተሰቡ በዓሉ ላይ እንዲገኝና በጀግናው የሀገር መከላከያ ሠራዊት አባል ሆነው ያገለገሉትንና እያገለገሉ ያሉ ጀግኖችን እንዲያከብር፣ እንዲዘክር፣ የሀገር መመኪያና ኩራት የሆነው ተቋም እንዲመለከትና በዚህ አስደናቂና ታሪካዊ በዓል ላይ እንዲታደም የኢትዮጵያ አየር ኃይል ጥሪውን አቅርቧል፡፡