ቀጥታ፡

በኦሮሚያ ክልል ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ወስደዋል

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል 956 ሺህ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸውን የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን አስታወቀ።

ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የመንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረግ አንዱ ነው።

ለዚህም ይረዳ ዘንድ ከመደበኛው የቴክኖሎጂ ትምህርቶች በተጨማሪ የኢትዮ-ኮደርስ እና የመሳሰሉ የበየነ መረብ የክህሎት ስልጠናዎችን መንግስት እንደ አማራጭ ለዜጎች ምቹ ማድረጉ የዚሁ ጥረት አካል ነው።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረውና ለ5 ሚሊዮን ዜጎች የተመቻቸው የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በሁሉም ክልሎች በተለያዩ ዙሮች እየተሰጠ ይገኛል።

በኦሮሚያ ክልልም ስልጠናው ከተጀመረ ወዲህ ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የእድሉ ተጠቃሚ በመሆን በርካቶቹ በዘርፉ ሥራ እስከ መፍጠር መድረሳቸው ተገልጿል።

የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ጅማ ቱሉ ለኢዜአ እንደተናገሩት በክልሉ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠናው ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ስራዎች ተሰርተዋል።

የስልጠናው ዓላማ ዜጎች በዲጂታል ዘርፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ከማድረግ ባለፈ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚያግዛቸው ጠቁመዋል።

በተጨማሪም ስልጠናው ተማሪዎች ከቴክኖሎጂ ጋር ያላቸው ግንኙነት የጠበቀ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ሲሆን ለስራ ፈላጊዎች ደግሞ እድላቸውን የሚያሰፋ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እቅዱን ለማሳካት የግንዛቤ ፈጠራ፣ ቤተ ሙከራዎች የማዘጋጀት፣ ኮምፒዩተሮችና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን የማሟላት እንዲሁም የስልጠና ማዕከላትንና ሌሎችንም የማመቻቸት ስራዎች በሰፊው መሰራታቸውን ገልጸዋል።

በክልሉ ዞኖችና ከተሞች ለመንግስት ሰራተኞች፣ ነጋዴዎች፣ ለአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች፣ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች የተመረቁ ተማሪዎች በስልጠናው በንቃት እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል።

በአጠቃላይ በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዜጎችን የስልጠናው ተጠቃሚ ለማድረግ የታቀደ ሲሆን እስካሁን 956 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል።

በብሔራዊ መታወቂያ የምዝገባ ስራ ላይ በርካታ ሰልጣኞች በቀጥታ ተሳታፊ በመሆን የስራ እድል ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙም አብራርተዋል።

በተያዘው በጀት አመት በክልሉ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የተቀመጠውን ዕቅድ ለማሳካት ርብርቡ እንደሚቀጥልም ኢንጂነር ጅማ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም