ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 1/2018(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው ሲሉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ።
ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል።
በጉባኤው ማጠናቀቂያ ንግግር ያደረጉት የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እያስመዘገበች ያለችው ዕድገት አስደናቂ ነው።
አሁን ላይ አብዛኛው ዜጋ ከፍተኛ መጠን ያለው ጥሬ ገንዘብ መያዝ አቁሟል ያሉት ገዥው፤ ኢትዮጵያውያን የዲጂታላይዜሽን እና የዳታ ሽግግርን በፍጥነት እየተላመዱ እንደሚገኙም አስረድተዋል።
ባለፉት አምስት ዓመታት በተዘረጋው የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት በየዓመቱ ከ18 ነጥብ 5 ትሪሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ዝውውር መከናወኑን ተናግረዋል።
ይህን የገንዘብ ዝውውር በጥሬ ገንዘብ ቢከናወን ከፍተኛ ወጪና መጨናነቅ ይፈጥር እንደነበር ጠቁመው፤ ይህ ስኬት ከጥቂት ዓመታት በፊት ፈጽሞ የማይታሰብ እንደነበር ጠቅሰዋል።
የመሠረተ ልማትን ለማስፋፋት የተሰጠው ትኩረት ዋነኛ የስኬቱ መገለጫ መሆኑን ገልጸዋል።
መንግሥትን ወደ ዲጂታል ግብይት እና የገንዘብ ዝውውር አገልግሎት ለማሸጋገር የሰጠው ትኩረት ለተመዘገበው ውጤት ትልቅ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰው፤ በትክክል የታሰበበት፣ በጥንቃቄ የተቀረጸና ተግባራዊ የተደረገ የስትራቴጂ ውጤት ስለመሆኑም ጠቁመዋል።
እስካሁን የተገኘውን ውጤት ይበልጥ ለማጎልበት እንደሚሰራ ጠቁመው፤ ውጤቱ የሚያዘናጋ ሳይሆን መስፈንጠሪያ ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል።
በቀጣይ የዲጂታል ባንኪንግ ተጠቃሚዎችን እምነት ለማሳደግ እና የሥርዓቱን ደኅንነት ይበልጥ ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ጠቅሰው፤ በገጠርና በከተማ ያለውን የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ልዩነት ለመቀነስ ይሠራል ብለዋል።
እንዲሁም የፈጠራ ሥራዎችን በበቂ ሀብት የመደገፍ ሥራዎች ወሳኝ በመሆናቸው በልዩ ትኩረት ይሠራል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በቁርጠኝነት ሠርታ ያስመዘገበቻቸው ትላልቅ ውጤቶች በቀጣዮቹ ዓመታት ለማሳካት ያስቀመጠቻቸውን ግቦች ለማሳካት ትልቅ መሠረት የሚሆኑ ናቸውም ብለዋል።
ኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት ትክክለኛ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመቅረፅ ትክክለኛውን እርምጃ መውሰዷንም ገልጸዋል።
ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ የመረጃ መሠረተ ልማትን ለማጠናከር፣ የዲጂታል ክፍያ እና ሰፋፊ የዲጂታል ስትራቴጂዎችን ለማስገንዘብ ሰፊ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለማስፋፋት መንግስት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚህም በርካታ ኢንቨስትመንት መከናወኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እንዲስፋፋ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይ ትኩረት ከሚሰጣቸው ተግባራት መካከል የመረጃ ሉዓላዊነት ጉዳይን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በብዙ መልኩ ኢንቨስት እያደረገች እንደምትገኝም አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ እንደምትገኝም ጠቁመዋል።
ከ2026 -2030 የሚተገበረው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ በሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ይፋ መደረጉን ይታወቃል።