ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ ነው  

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር ከኢኮኖሚው ጋር አብሮ እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ ገለጹ።

የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሊየር ኃይል መርሃ ግብር ሚና እና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት የምክክር መድረክ ሁለተኛ ቀን ቀጥሏል።


 

የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኅይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኒውክሊየር ኃይል ተፈጥሮ ለአንድ ሀገር ዘላቂ ልማት እና እድገት ወሳኝ ነው።

ኢትዮጵያ የምትከተለው አረንጓዴ ኢኮኖሚ መሆኑን ገልጸው፤ የኢንዱስትሪዎቿ ቁጥር እና ዓይነት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ ወደ ኋላ እንዳይመለስ የኃይል ምንጭን አስቀድሞ ማዘጋጀት ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት ምላሽ መስጠት የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አብዱረዛቅ ኡመር በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከአካባቢ ጥበቃ ጋር የተስማማ በቂ እና አስተማማኝ ኃይል ለኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ወደ ፊት መራመድ እንደምትፈልግ ተናግረዋል።


 

የኢትዮጵያን ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይል አማራጭ የሀገሪቱን የልማት ትልሞች የሚያሳካ መሆኑን ጠቁመዋል።

በመካሄድ ላይ ባለው ዓውደ ጥናት የተለያዩ ሀገራት ልምድ እና ተሞክሮዎች ቀርበው ውይይት እየተደረገባቸው መሆኑን ገልጸዋል።

እንዲሁም አንድ ሰላማዊ የኒውክሊየር መሰረተ ልማት ለማቋቋም መከናወን ባለባቸው ተግባራት ላይ ግንዛቤ እየተፈጠረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም