ቀጥታ፡

የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከባንክ ስርዓት ጋር የማጣመር ሥራ በይፋ ተጀመረ

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ):- የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከባንክ ስርዓት ጋር የማጣመር ሥራን ዛሬ በጋራ ማስጀመራቸውን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም አስታወቁ።

ሁለቱ ተቋማት ባወጡት የጋራ መግለጫ ፋይዳ ዲጂታል የማንነት መረጃ ከሁሉም ባንኮች የደንበኞች ባንክ ሂሳብ ቁጥር ጋር የማጣመር (Harmonization) ስራን በይፋ መጀመሩን ገልጸዋል።

ይህ የመረጃ ሥርዓቶችን የማጣመር ስራ ደንበኞች ባሉበት ቦታ ሆነው ደህንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ገንዘብ ማስተላለፍ እንዲችሉ፣ በሀሰተኛ ሰነድ የራሳቸውን ሂሳብ ሌሎች ማንቀሳቀስ እንዳይችሉ፣ በቀላሉ የብድር አገልግሎትን ማግኘት እንዲችሉ እና በአንድ ፋይዳ መታወቂያ የሁሉንም ባንክ ሂሳብ መጠቀም እንዲያስችላቸው ተመላክቷል።

ባንኮች በዚህ መረጃ ጥምረት የደንበኞቻቸውን ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃን እንዲያገኙ፣ በሀሰተኛ ማንነት የሚከሰት የገንዘብ መጭበርበርን ከመከላከል ባለፈ ለፋይናንስ ሴክተር ዲጂታል ትግበራ ቁልፍ የዲጂታል መሰረተ ልማት ሆኖ እንደሚያገለግል መግለጫው ያትታል።

ይህን የባንክ ሂሳብ ቁጥር ከፋይዳ መረጃ ጋር ለማጣመር ደንበኞች ወደ ባንክ ቅርንጫፎቻቸው በአካል በመሔድ ወይም ኦንላይን(ባንኩ በሚያስቀምጠው አሰራር መሰረት) የፋይዳ ተለዋጭ ቁጥር (16 አሀዝ-FAN Number) በማቅረብ ማከናወን ይችላሉ።

ደንበኞች በተጠቀሰው የጊዜ ገደብ ማለትም እስከ መጋቢት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የባንክ ሂሳባቸውን ከፋይዳ መረጃ ጋር እንዲያጣምሩ ብሔራዊ ባንክ አሳስቧል።

ለፋይዳ ያልተመዘገበ ማንኛውም የባንክ ደንበኛ በቅድሚያ በአቅራቢያው በሚያገኘው የፋይዳ ምዝገባ ጣቢያ በመሄድ መመዝገብ እንዳለበትና ባንኮች በዚህ ሂደት ደንበኞች መጉላላት እንዳያጋጥማቸው አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ በመፈፀም ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል።

በሁሉም ባንኮች አዲስ ሂሳብ መክፈት(New Account Opening) (በ “VeriFayda 2” እንዲጀመር፣ እንዲሁም ነባር ሂሳቦችን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር ማስተሳሰር (Existing Account Harmonization) ትግበራም በ “VeriFayda 2” ተግባራዊ የሚደረግበት የጊዜ ሰሌዳ ወጥቶ ለሁሉም ባንኮች ህዳር 25 ቀን 2018 ዓ.ም መሰራጨቱ በመግለጫው ላይ ሰፍሯል።

ቀደም ሲል ሁሉም ባንኮች አዲስ ሂሳብ ለመክፈት የ VeriFayda 1 ስርዓትን ሲጠቀሙ መቆየታቸውም ተመላክቷል፡፡

ከዚህ በኋላ ባንኮች ይበልጥ ዘመናዊና የተቀናጀ ወደ ሆነ ስርዓት “VeriFayda 2” (በኢቲስዊች - EthSwitch በh-A eKYC Service) የማሸጋገር ሥራን በተሳካ ሁኔታ እንዲያከናውኑ የፕሮግራሙና የኢቲስዊች የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች ለባንክ ተቋማት የቴክኒክ ድጋፍ እና ክትትል እያደረጉ ይገኛል።

በቀጣይም የቴክኒክ ድጋፉ እንደሚቀጥል ባንኩ አስታውቋል።

በተመሳሳይ ሁሉም ባንኮች ለደንበኞቻቸው አዲስ የባንክ ሂሳብ ለመክፈትም ሆነ ከነባር ሂሳብ ጋር የማጣመር ስራን በመስራት ከVeriFayda 1 (old eKYC) ሙሉ በሙሉ ወደ VeriFayda 2 (new eKYC Service) መሸጋገር እንደሚኖርባቸው ባንኩ አሳስቧል።

ይህንን ተከትሎ ቀደም ሲል ባንኮች ሲጠቀሙበት የነበረው የ VeriFayda 1 (eKYC Service) ስርዓት አገልግሎት መስጠት እንደሚያቆምም አመልክቷል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ይህን የማጣመር ስራ በፍጥነት ወደ ትግበራ ማስገባታቸው ለፋይናንስ ዘርፉ ብቻ ሳይሆን ሀገሪቱ ወደ ትራንስፎርሜሽን በምታደርገው ጉዞ ላይ ትልቁን ሚና እንደሚጫወት ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም