በምዕራብ ሸዋ ዞን የአፈር አሲዳማነትን በኖራ በማከም ከገብስ ልማት የተሻለ ምርት ይጠበቃል - ኢዜአ አማርኛ
በምዕራብ ሸዋ ዞን የአፈር አሲዳማነትን በኖራ በማከም ከገብስ ልማት የተሻለ ምርት ይጠበቃል
አምቦ፤ ታህሳስ 01/2018 (ኢዜአ)፡-በምዕራብ ሸዋ ዞን በአፈር አሲዳማነት የተጠቃን መሬት በኖራ በማከም በተካሄደ የገብስ ልማት የተሻለ ምርት እንደሚጠበቅ የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ።
የኦሮሚያ ክልል እና የዞኑ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዞኑ ወልመራ ወረዳ የገብስ ምርት አሰባሰብ ሂደትን ተመልክተዋል።
በዚሁ ጊዜ የምዕራብ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በዞኑ በተለይም በአፈር አሲዳማነት የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም በገብስ የማልማት ስራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል።
ባለፈው መኸር አዝመራ በገብስ የለማው ከዚህ በፊት እጅግ ዝቅተኛ ምርት የሚሰጥ በመሆኑ የዞኑ አርሶ አደሮችም መጠቀም አልቻሉም ነበር ብለዋል።
መሬቱ በኖራ ከታከመ በኋላ ከአንድ ሄክታር መሬት እስከ 50 ኩንታል የገብስ ምርት እየተገኘ መሆኑን ጠቅሰው ይህም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ብቻ ሳይሆን ከውጪ የሚገባውን የቢራ ገብስ ለመተካት ያግዛል ነው ያሉት።
በዚህም በዞኑ 48 ሺህ ሄክታር በቢራ ገብስ የለማ ሲሆን ከለማው መሬት ላይም 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚሰበሰብ ገልጸዋል።
አርሶ አደሩ ለተመረተው ምርትም የገበያ ችግር እንዳይገጥመው ከዩኒየኖች እና ከኬኛ ቢቨሬጅ ጋር የገበያ ትስስር ስምምነት መፈጸማቸውንም አስረድተዋል።
በወልመራ ወረዳም በተገባው ውል መሰረት በአርሶ አደሮች የቀረበ 578 ኩንታል የቢራ ገብስ ለዩኒየኖች መቅረቡን ጠቁመዋል።
የወልመራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጋሪ በበኩላቸው፤ በወረዳው ከአርሶ አደሩ ጋር በቂ ውይይት ከተደረገ በኃላ በአሲድ የተጎዳውን መሬት በኖራ በማከም ወደ ምርት ማስገባት መቻሉን ተናግረዋል።
ለመኸር አዝመራ ዝግጅትም 18 ሺህ ኩንታል ኖራ መከፋፈሉን ጠቅሰው ምርጥ ዘር እና የአፈር ማዳበሪያ በጊዜ በመቅረቡ የተሻለ ምርት እየተሰበሰበ ይገኛል ብለዋል።
በወረዳው በመኸር አዝመራ 70 ሄክታር መሬት የቢራ ገብስ በማልማት ምርቱን በኮምባይነር ታግዞ እየተሰበሰበ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የወልመራ አርሶ አደሮችም በመኸር አዝመራ በኩታ ገጠም ያመረቱትን ገብስ ለገበያ እንዲያቀርቡ እድል መመቻቸቱ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያጎለብት ገልጸዋል።
ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል ደሲሳ ረጋሳ እንዳሉት፤ መሬታቸው በአሲድ የተጠቃ በመሆኑ የሚያገኙት ምርት ዝቅተኛ ነበር።
ባለፈው ዓመት መሬቱን በኖራ ማከም በመቻላቸው ከአንድ ሄክታር መሬት 53 ኩንታል የገብስ ምርት ማግኘታቸውን አውስተዋል።
መሬታቸውን በኖራ በማከምና ምርጥ ዘር እና ማዳበሪያ በአግባቡ በመጠቀማቸው የተሻለ ምርት ማግኘት መጀመራቸውን የገለጹት ደግሞ አርሶ አደር አሰፋ አንጋሱ ናቸው፡፡