ቀጥታ፡

የከተማ ግብርና የዜጎችን ጤናማ የአመጋገብ ሥርዓት ከማሻሻል ባለፈ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እየሆነ ነው

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- የተቀናጀ የከተማ ግብርና የዜጎችን ጤናማ የአመጋገብ ሥርዓት ከማሻሻል ባለፈ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ መሆኑን የተለያዩ የጤና ተቋማት ገለጹ፡፡

በመዲናዋ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት በከተማ ግብርና በመሰማራት ጤናማ የአመጋገብ ስርዓትን መፍጠር የሚያስችሉ ውጤቶችን እያስመዘገቡ ነው፡፡

ኢዜአ በኢትዮጵያ የአካል ድጋፍ አገልግሎትና በሎሚ ሜዳ ጤና ጣቢያ በተቀናጀ የከተማ ግብርና ልማት ላይ ቅኝት በማድረግ የተቋማቱን ሰራተኞችና የሥራ ኃላፊዎችን አነጋግሯል፡፡

የኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ ብሩክ ነጋሽ እንዳሉት፤ በአገልግሎቱ የሚከናወነው የተቀናጀ የከተማ ግብርና ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው፡፡ 


 

በወተት ላሞችና በዶሮ እርባታ፣ በንብ ማነብ እንዲሁም በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት በመሰማራት የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደሆናቸው ገልጸዋል፡፡

በአገልግሎቱ የተጀመረው የተቀናጀ የከተማ ግብርና ለታካሚዎች የተመጣጠነ ምግብ ማቅረብ አስችሏል ብለዋል፡፡

የሎሚ ሜዳ ጤና ጣቢያ ሜዲካል ዳይሬክተር መኪያ አብደላ በበኩላቸው፤ በጤና ጣቢያው የከተማ ግብርናን ከጀመሩ ሶስት ዓመታት ማስቆጠራቸውን ገልጸዋል፡፡


 

በጤና ጣቢያው በተጀመረው የተቀናጀ የከተማ ግብርና የዕለት የምግብ ፍጆታቸውን ከማሟላት ባሻገር ለአካባቢው ማሕበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ የከተማ ግብርና ልማት በጤና ጣቢያው ምቹ እና ጤናማ የሆነ የስራ ከባቢን መፍጠር አስችሏል ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት የጠቅላላ አገልግሎት ሰራተኛ ፊጣ ታደሰ፤ በተቀናጀ የከተማ ግብርና ስራ የተለያዩ አትክልትና ፍራፍሬዎችን እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል፡፡


 

የሎሚ ሜዳ ጤና ጣቢያ የህክምና ባለሙያ ሲስተር ፍሬህይወት መላኩ፤ የጤና ጣቢያው የከተማ ግብርና ከምግብ አገልግሎት ባለፈ አካባቢውን አረንጓዴ በማልበስ ለታካሚዎች ሳቢ ከባቢ መፍጠር አስችሏል ብለዋል፡፡


 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአርሶ አደር እና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽነር ባዩ ሽጉጤ በበኩላቸው፤ በመዲናዋ ከሁለት ሺህ 600 በላይ ተቋማት በተቀናጀ የከተማ ግብርና እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡


 

ከእነዚህ ውስጥ ከ102 የሚልቁት የጤና ተቋማት መሆናቸውን ገልጸው፤ በዘርፉ ለተሰማሩ ተቋማት የሥልጠናና የግብዓት ድጋፍ እናደርጋለን ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም